ማክሰኞ 20 ኖቬምበር 2018

+ + + የመላእክት ተፈጥሮ + + +


                          በዲያቆን መልአኩ ይፍሩ

ውድ የሥላሴ ልጆች፣ የሥላሴን የቸርነቱን ፏፏቴ የምሕረቱንም ውቂያኖስ ለማየት እና በዚያም ሰጥሞ በፍቅር ለመቅረት የምንሻስ ከሆን ፍጡራንን ለምን ፈጠረ ብለን እንጠይቅ። መልሱን ስንፈልግ ቸርነቱ ጋር እንደርሳለንና። ሥላሴ ፍጡራንን ሊፈጥር የሳበው ፍቅሩ እና ቸርነቱ እንጂ ምንም ምን ሌላ አይደለምና።

+ መላእክት የምንላቸው ከሀያ ሁለቱ ሰናያን ፍጡራነ እግዚአብሔር መኻከል አንደኞቹ ናቸው። ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ሊቁ በመጽሐፈ አክሲማሮስ እንደሚነግረን፣ ሥላሴ ቅድመ ዓለም በባህርዩ ምስጉን ሁኖ ሲኖር ክብሩ በርሱ ብቻ እንደቀረ ዐይቶ ፍጡራንን ይፈጥር ዘንድ አሰበ። አስቦም አልቀረ በሦስተ መንገድ እና በስድስት እለታት ሀያ ሁለት ወገን አድርጎ ቁጥር የማይገኝላቸውን ፍጡራን ፈጠረ።
      የፈጠረባቸውም ሦስት መንገዶች እሊህ ናቸው፥
  1/ በሀልዮ (በማሰብ)፥ በዚህ መንገድ የፈጠረው ሰባት ፍጥረት ሲሆን ይህን መንገድ የፈጠረበት ሰማዕያን የሆኑት ፍጡራን መላእክት እስኪገኙ ድረስ ነበር።
  2/ በነቢብ (በመናገር)፥ ይህን መንገድ ደግሞ አሥራ አራት ፍጡራንን ፍርጥሮበታል። ይኸውም ከላይ ባለ'ው መንገድ ሰማዕያን ለባውያን የሆኑ ፍጡራን (መላእክት) ተገኝተዋልና በነቢብ መፍጠር ጀመረ።
  3/ በገቢር (በመሥራት)፥ በዚህ መንገድ የተፈጠረው ልዩው ፍጡር አንድ ፍጡር ብቻ ነው።

በእሊህ ሦስት መንገዶች ከተፈጡሩት ፍጡራን ወገን ለባውያን (reasonable beings) የሆኑት እና ሥላሴን አመስግነው ከክብረ ሥላሴ ለመውረስ የተፈጠሩት ሁለት ፍጡራን ብቻ ናቸው። እነርሱም መላእክት እና የሥላሴ አርአያ የተሰጠው የሰው ልጅ ናቸው። የሰው ልጅን ጉዳይ ከዚህ አቆይተን ስለመላእክት እንነጋገር።

¶ መልአክ፥  በግእዙ "ለአከ- ላከ" ካለው ግሥ የተገኘ ሲሆን መልእክተኛ ማለት ነው። ይኸውም የፍጡራንን (የሰው ልጆችን ልመና) ቅድመ መንበረ ሥላሴ የሚያሳርጉ፣ የሥላሴን የምሕረትና የቸርነት ስጦታ ወደ ፍጡራን የሚያደርሱ ናቸው።

መላእክት የተፈጠሩት በእለተ እሑድ ሲሆን የተፈጠሩትም ከእሳትና ከነፋስ ነው። ይህም ሲባል አክሲማሮስ እንደሚነገረን ግብራቸውን ማለትም እንደእሳት ረቂቅ እንደነፋስ ፈጣን ለማለት እንጂ ከባህርየ ሥጋ ተፈጥረውስ ቢሆን መፍረስ መበስበስ ባገኛቸው ነበር። ቄርሎስ ዘኢትዮጵያ የተባለው ሊቅ "ዘይሬስዮሙ ለመላእክቲሁ #መንፈሰ ወለእለ ይትለአክዎ #ነደ እሳት- መላእክቱን #መንፈስ (እምደነፋስ ቀሊላን ረቂቃን) የሚላኩትንም #የእሳት ነበልባል የሚያደርጋቸው " እንዳለው በሰአታቱ። ስለዚህም እም ኀበ አልቦ ኀበ ቦ (ካለመኖር ወደ መኖር) አምጥቶ ፈጥሯቸዋል። ሲፈጥራቸው አስቀድሞ መኖሪያቸው ሰማያትን አዘጋጅቶ ነው። ስለዚህ ጉዳይ ሊቁ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ እንደሚለን ሥላሴ ሰማያትን አስቀድሞ መፍጠሩ፥
    ሀ/ መላእክትን አስቀድሞ ፈጥሮ ቢሆን "እርሱ ሲመሠረት እኛ ሌላውን ሠራን፥ እሱ ሲመሠረት አብረን መሠረትን" ባሉ ነበርና ይህችን ድኩም ሕሊና ከመላእክት ለማጥፋት ቀድሞ ሰማያትን ፈጠረ። ይኸውም ይታወቅ ዘንድ አቡሃ ለሐሰት የተባለ እኩይ ዲያብሎስ ከሰማያት በኋላ ተፈጥሮም እንኳን "እኔ ፈጣሪ ነኝ" ብሏልና።
   ለ/ ዳግመኛም ዛሬ አንድ እንግዳ የሚጠራ ሰው ለእንግዳው የሚሆነውን ማደሪያ ሳያዘጋጅ እንዳይጠራው፣ እንዲሁ ሁሉ ሥላሴም የመላእክትን ማደሪያቸውን መኖሪያቸውን አዘጋጅቶ መላእክቱን መፍጠሩ እንዴት የተገባ እንደሆነ ልብ እንበል።

+ #መላእክት ተፈጥሯቸው እንዲህ ሁኖ ሲፈጠሩ፥ በአጠቃላይ መቶ ነገደ መላእክት እና አሥር ሊቃነ መላእክት ሁነው ነበር። እሊህንም ሦስቱን ሰማያት #ኢዮር፣ #ራማ እና #ኤረርን ከአሥር ከተማ አድርጎ ከፍሎ በዚያ አስቀምጧቸዋል።

+ አሥር አሥሩን ነገደ መላእክት አንድ አንድ አለቃ እየሾመ በየከተማው አኑሯቸዋል። የነገደ መላእክቱ ስምም ከላይ ወደ ታች ይህ ነው።

  ° አጋእዝት፥ አለቃቸው ሳጥናኤል(ነበረ)
  ° ኪሩቤል፥ አለቃቸው ኪሩብ ሲሆን በዐይን የተሸለሙ የካህናት አምሳል የሆኑ ነገደ መላእክት ናቸው።
  ° ሱራፌል፥ አለቃቸው ሱራፊ ሲባል ስድስት አክናፍ እና ስድስ እጆች ያሏቸው ነገደ መላእክት እሊህ ናቸው።
  ° ኃይላት፥ አለቃቸው #መልአከ ኃይል #መልአከ ምክር #መጋቤ ብሉይ ቅዱስ ሚካኤል ነው። ሰይፍን የሚይዙ ሊቃነ መላእክት እሊህ ናቸው። እሊህን አራቱን ሊቃነ፡መላእክት እና አርባውን ነገድ በኢዮር ሰማይ ላይ ኢዮርን አራት ከተማ አድርጎ ከላይ ወደታች አኖራቸው።

  ° አርባብ፥ አለቃቸው መልአከ ብሥራት ቅዱስ ገብኤል ሲሆን የሥላሴ አጋፋሪ፣ እልፍኝ አስከልካዮች ይላቸዋል አክሲማሮስ።
  °መናብርት፥ የእነዚህ አለቃቸው ቅዱስ ሩፋኤል ሲሆን አክሲማሮስ እንደሚነግረን ሀያ አራቱን ካህናተ ሰማይ የተመረጡት ከእነዚህ ነገደ መላእክት ነው።
  ° ስልጣናት፥ አለቃቸው መልአከ ጥበብ ከሣቴ ምስጢራት መራሔ ብርሃናት የሆነው ቅዱስ ዑራኤል ሲሆን እሊህን የሥላሴ ነጋሪት መችዎች ለስባሔ የሚያነቁ ይላቸዋል። እሊህን ሦስቱን ሊቃነ መላእክት እና ሠላሳውን ነገደ መላእክት በራማ ሰማይ ላይ ራማን ከሦስት ከተማ አድርጎ ከፍሎ በዚያ አኑሯቸዋል።

  ° መኳንንት፥ እሊህ ደግሞ አለቃቸው መልአኩ ሰዳክያል (ሰዳካኤል) ይባላል።
  ° ሊቃናት፥ አለቃቸው መልአኩ ሰላትያል (ሰላታኤል) ይባላል።
  ° መላእክት፥ አለቃቸው መልአኩ አናንያል (አናንኤል) ይባላል። እዚህ ጋር "መላእክት" ብለን የተናገርነው የነገዱ ስም መሆኑን ልብ ይሏል።

+ እኒህ ረቂቃን ፍጡራን የተለያየ ዓይነት፣ የተለያየ ተፈጥሮ አላቸው። ይኸውም ማለት በክንፋቸው ሀገራትን አኅጉራትን የሚሸፍኑ፣ ቁመታቸው ከጠፈር እስከ በርባሮስ (መሠረተ ምድር) ድረስ የሚደርሱም አሉ። ልዩ ልዩ ዓይነት ናቸው።
+ ሌላኛው ነገር፣ መላእክት ለተልእኮ ካልሆነ በቀር ሥላሴ ካስቀመጣቸው ቦታ በፍጹም አይወጡም። በዚህም ተልእኳቸው ምክንያት በተለያየ ጊዜ ወደ ሰው ልጆች ተልከው በሠሩት ስራ የሚዘከሩ መላእክት አሉ። ለምሳሌም ያህል ብናነሳ ወደ ታላቁ የእግዚአብሔር አፍ ወደ መጽሐፍ ቅዱስ እንሂድ።
  - መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል ወደ ጦቢትና ቤተሰቦቹ ተልኮ እንደነበረ እና ስላደረገላቸው ድንቆች በመጽሐፈ ጦቢት እንመለከታለን
  - መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል በተለያየ ጊዜ እስራኤልን ሲመራቸው፣ ወደ ዳንኤል ሲላክ፣ ወደ ጌድዮን ወደ ሌሎቹም ሲላክ እናነባለን።
- መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልም ሠለስቱ ደቂቅን ለማዳን፣ ዘካርያስን ለማብሠር፣ ከሁሉም፡በላይ ደግሞ የሰው ልጆች ስንናፍቀው የነበረውን ደስታ ለማብሠር ወደ አዛኝቷ የማሂት ርግብ ተልኮ ሲሄድ እንመለከታለን።

+ በተፈጥሯቸው መላእክት ያገቡም አይጋቡም። ምክንያቱም ጾታም የላቸው። አንድ ጊዜ እልፍ አእላፋት ወትእልፊተ አእላፋት ተደርገው መቁጠር በማይቻለን መጠን አብዝቶ ፈጥሯቸዋል። እርሱ ግን እያንዳንዳቸውን በስማቸዋ ያውቃቸዋል። እጹብ ድንቅ፡ነው።

ይቆየን።
©ዘዲያቆን መልአኩ ይፍሩ
ከዲያቆን መልአኩ ይፍሩ ዘውሉደ ብርሃን የመልአኩ ቅዱስ ሚካኤልን የሲመት ክብረ በዓል በማስመልከት ተጻፈ።
ኅዳር ፲፪፣ ፳፻ወ፲፩ ዓ.ም
ሲቹዋን ቸንዱ፣ ቻይና

እሑድ 18 ኖቬምበር 2018

🤲የኛስ የጸሎት ሕይወት . . . ?!🤲

🙏 "ጌታችን (ቅዱስ እንጦንስን) በጸሎቱ ሁልጊዜም ደስተኛ እንዲሆን አድርጎታልና ጸሎታቱ በተሰሙለት ጊዜ በልቡ ከልክ በላይ ከፍ ከፍ የሚል ስሜት(ትዕቢት) አልነበረም፤ እንዲሁም ባልተሰሙለት ጊዜም እንኳ ፈጽሞ አያጉረመርምም ነበር፤ በሁሉም እግዚአብሔርን ያመሰግናል እንጂ"
               /መጽሐፈ ገነተ አበው ቅዱሳን
              Paradise of the holy Fathers/
  ©ዘዲያቆን መልአኩ ይፍሩ
   ኅዳር ፱/፳፻ወ፲፩ ዓ.ም
    ሲቹዋን ቸንዱ፣ ቻይና

ዓርብ 16 ኖቬምበር 2018

ሔዋኔ

ሔዋኔ!
(በዲያቆን መልአኩ ይፍሩ)

እግዚአብሔር አክብሮኝ ከፍጥረታቶቹ፣
በአርአያው በአምሳሉ ሠርቶኝ በእጆቹ፣
ስኖረ በገነት ውስጥ እርሱ እንደፈቀደ፣
ብቻዬን ነኝና ሔዋንን ከጎኔ ሊፈጥር ወደደ።

ታዲያም
በማእከለ ነዊም ወነቂህ ሳለሁኝ፣
ከጎኔ አጥንት ወስዶ አጋር ፈጠረልኝ፣
አጥንትሽ ከአጥንቴ ሥጋሽ ከሥጋዬ፣
መሆኑን አውቄ ጠራሁሽ ሴት ብዬ።

አምላክም
ትዕዛዝን ሰጠኝ በርሱ እንድታመን፣
ፍጡር ለፈጣሪው ይታዘዝ ዘንድ ሲሆን፣
ከገነት ዕፅዋት ሁሉ ተፈቅዶልኝ፣
አንዲቱ በለስ ግን ለሕግ ተሰጠችኝ።

በዚህም ታምኜ ሰባት ዓመት ኖሬ፣
በእባብ አድሮ መጣ ያ ርኲስ ክፉ አውሬ፣
ወደኔ ቢመጣ፣
ሊያስተኝ ቢቃጣ፣
እኔ ሳሳፍረው አንቺ ተቀበልሺው፣
ምን ነበር ሔዋኔ ምክሩንስ ባትሰሚው?!
ከገነት ተባረርኩ፣
ከዕፀ ሕይወትም እንዳልበላ ታገድሁ።

አይ ሔዋን!?
በመጨረሻው ሰዓት ደግሞ በሱባዔ
ንስሓ ገብቼ ልታረቅ አምላኬን
ዲያብሎስ መጣና ገብርኤል ነኝ ብሎ፣
አሁንም ሲጠራኝ የተላከ መስሎ፣
አልቀበል ብለው ወዳንቺ ሲመጣ፣
ፈጥነሽ ለቀሽ ወጣሽ ምሕረት ሳይመጣ።

እሺ!
እሺ ይሁን ብዬሽ ተቀብለን ሄደን፣
ከገነት መግቢያዋ ከደጃፏ ደርሰን፣
ዲያብሎስ መሆኑን ገልጦ ነገረን፣
ምናለ ሔዋኔ አሁንስ ቢበቃን?

ግና!   . . . . ግና!
አምላክ መድኃኔዓለም መሐሪ ነውና
መቶ ዓመት ጸሎት ሱባዔ ገብቼ፣
የኛን በደል ሊፍቅ በልጅ ልጅ ልጆቼ፣
ቃልኪዳን ገባልኝ መጣሁ ተደስቼ።

ሔዋኔ!
አሁን ላመስግንሽ
በክራር መሰንቆ ዜማ ልቀኝልሽ።

ቀድሞ በበደልሽ እጅጉን ሳማርር፣
አምላክን ወለድሽው በዚህች ትንሽ ምድር?!
ወይ ተአምር!
በአንቺው ወድቄ በአንቺው ልድን ነው?
አቤት አቤት አንተው!

አምላኬ ሆይ
ቸርነት ምሕረትህ ብዙ ነበር ለካ፣
በሔዋን ጠፍቼ ደግሜ በርሷ ልተካ፣
አምላክን ታቅፈሽ ጡትሽን አጥብተሽ፣
የሕይወቴን ብርሃን ይኸው ወልደሽ ሰጠሽ።

ሔዋኔ!

አሁን ላመስግንሽ፣
በክራር መሰንቆ ዜማ ልቀኝልሽ!

የተገባልኝ ቃል አምስት ቀን ተኩል፣
እንሆ በአንቺ ይኸው ተፈጽሟል።
ይደንቃል!

በአንቺ ምክንያት የሞት ሞትን ሞትኩኝ፣
ዳግመኛም በአንቺ ሕይወት አገኘሁኝ፣
እግዚአብሔር ይመስገን አንቺን ስለሰጠኝ፣
በአንቺም ምክንያት ከሞት ስላዳነኝ።
ፍጥረት ዘመረልሽ፣
አምላክ በመውለድሽ፣
ሕይወት በመያዝሽ፣
ድኅነት ስላመጣሽ፣
ሔዋኔ
አሁን ላመስግንሽ፣
በክራር መሰንቆ ዜማ ልቀኝልሽ።

ተጻፈ፡ በዲ/ን መልአኩ ይፍሩ ዘውሉደ ብርሃን
          ፳፻ወ፩ ዓ.ም
(የመጀመሪያ ደረጃ ተማሪ እያለሁ ከጻፍኋቸው አንዲቱ። ለጊዜው ከመጻፍ ጋር ብንራራቅም ታነቧት ብዬ አጋራኋት።)

©ዲያቆን መልአኩ ዘውሉደ ብርሃን

ረቡዕ 14 ኖቬምበር 2018

በእንተ ጻድቃን

👉" ጻድቅን የሚጠላ በርሱ ያደረውን እግዚአብሔር ይጣላል።"

       ❤️"ጻድቅን የሚያፈቅር በርሱ ውስጥ ባለው በእግዚአብሔር ፍቅር ሠክሮ ሥላሴን በማመስገን አይደክምም፤ ስለርሱም ስለእግዚአብሔር የሚመጣበትን መከራ ሁሉ ጻድቁን አብነት በማድረግ በአኰቴት ደስ እያለው ይቀበላል። በጻድቁ ምልጃና ጸሎት በእግዚአብሔርም ቸርነት ለድል አክሊል ይበቃል።"

ገባሬ መንክራት፣ ትሩፈ ምግባራት ወገድላት፣ ርዕሰ ባሕታውያን ጻድቅ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፡ተዘከረነ፡በጸሎትከ ቅድስት እንተ ትገብር ዐቢይ ኃይለ። አሜን።
©ዘዲ/ን መልአኩ
ኅዳር ፭፣ ፳፻ወ፲፩ ዓ.ም
ሲችዋን ቸንዱ፣ ቻይና

➕ቤዛዊተ ዓለም ወይስ የቤዛዌ ዓለም እናት ብቻ?!➕

በስመ አብ ወወልድ ወአንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

✍ይህ ነገር በተለይም ከኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውጪ ያሉ ወንድሞች የሚያነሱት አንዱ ጥያቄ ነው። ነገረ ድኅነትን፣ ምሥጢረ ሥጋዌን በተረዳ መንገድ ላገናዘበ ክርስቲያን ግን የሚከብድ ጥያቄም አይደለም።

ከቃሉ መሠረታዊ ትርጉም እንነሳና ወደታች በከፊል ጉዳዩን እንመልከተው።
   ቤዛ ፥ በቁሙ ዋጋ፣ ካሣ፣ ልውጥ ምትክ፣ ዐላፊ ዋቢ፣ ዋስ መድን፣ ተያዥ ጫማ ጥላ ጋሻ የመሰለው ኹሉ። "ቤዛ ነፍሱ ለብእሲ ጥሪተ ብዕሉ።" "አኮ በቤዛ።"  "ቤዛ ኲሉ ኃጢአትከ።"  "ማእስ ቤዛ ማእስ።"(ምሳ ፲፫፥፰፤ ኢሳ ፵፭፥፲፫፤ ኤር ፲፭፥፲፫፤ ኢዮ ፫፥፬)
   ቤዛ በሌላም ወገን በደቂቅ አገባብ ሲገባ ልዩ ትርጉም አለው። ይኸውም ከዚህ ብዙ የሚርቅ አይደለም። እሱም ስለ ፈንታ፣ ምክንያት ማለት ይሆናል። ይህም ማለት በምሳሌ ብናየው ጌታችን "እሜጡ ነፍስየ ቤዛ አባግዕየ" ሲል ይገኛል። ትርጉሙም "ነፍሴን ስለበጎቼ አሳልፌ እሰጣታለሁ" ማለት ነው።

የቤዛን ትርጉም ለመግቢያ በጥቂቱ ካልን፣ ይህን ያነሳነው በሰፊው ለመነጋገር አይደለምና ለሌላ ጊዜ እናቆየው። ወደ ተነሳንበት ነገራችን እንመለስና ትርጉሙን እናመሳክረው።

እመቤታችን ርኅርኅተ ኅሊናን ቤዛዊተ ዓለም ብለን እንጠራታለን።

👉ቤዛ ከላይ በመግቢያው እንዳየነው አንዱ ትርጉሙ ልውጥ ምትክ ማለት ነው። ይኸውም በአንዱ ፈንታ ሌላው ተገብቶ የዚያኛውን ዋጋ ሲከፍል፣ ዕዳውን ሲቀበል፣ በአጠቃላይ ልክ እንደዚያኛው ሰው ሁኖ የርሱ የሆነውን ነገር ሁሉ ሲተካ ቤዛ ተብሎ ይነገራል። "ከሴቶች ሁሉ ተለይተሽ አንቺ የተባረክሽ ነሽ" የተባለላት ብጽእት እመቤት ወላዲተ አምላክም ቤዛ ናት።
   + ቀዳሚት ሔዋን ድንግልና ሕሊናዋን ገሣ' ኃጢአትን ጸንሳ ሞትን ስትወልድ ዳግሚት ሔዋን የዋሂት ርግብ እመብርሃን ድንግል በክልኤ ሁና ጸንታ በመገኘት ሔዋን ያጣቸውን ድንግልና በርሷ ፈንታ ምትክ አድርጋ አቅርባለችና። የሔዋንን የድንግልና ካሣ በሔዋን ተገብታ መልሳለች። ሕዝ ፵፬፣ ኆኅት ኅትምት መባሏም አንዱ ለዚህ ነውና።

    + ሔዋን ድንግልናዋን አጥታ የወለደቸው ልጅ ወንድሙን የገደለ ነፍሰ ገዳይ ሆነ። እመብርሃን ግን በሔዋን ምትክ ሁና የወለደችው ልጅ ስለሁሉ ነፍሱን አሳልፎ የሚሰጥ፣ ንጉሥ ሁንክ ሳለ በአገልጋዮቹ የሚሰቃይ፣ ባዕለ ጠጋ ሁኖ ሳለ እንደምስኪን ድሃ የተቆጠረ ነውና። ይኸውም ስለ ድኅነተ ዓለም ነው።
   
ቤዛዊተ ዓለምና ስደቷ
    + ቀዳሚት ሔዋን በበደለችው እና ባስበደለችው በደል በሰው ልጆች ሁሉ ላይ ከመካነ ፍስሐ ገነት ስደት መጦብን ነበር። በዚህም ምክንያት በስደት ዓለም ስንቅበዘበዝ ዐይታ አንጀቷ የማይችል የዋሂት ርግበ ኤፍራታ ባለ ድንቅ መዐዛዋ የእሴይ አበባ ድንግል ልጇን ይዛ የሰው ልጆችን ስደት በሰው ልጆች ተገብ'ታ ተሰደደች። የሔዋንን ቁስል ቆሰለች፤ የሔዋንን ጥማት ከልጇ ከወዳጇ ጋር ተጠማች። በእውነት ያለሐሰት ይህን'ስ ላሰበው ሰው ሕሊናን የሚያናውጽ ምንኛ ከባድ ነው። ምስኪኗ የዋህ የሆነችው የ፲፭ ዓመቷ ሕጻን ድንግል ዳግሚት ሔዋን ሁና የሔዋንን ስደት ተሰደደች። በእውነት ይህን ርኅራኄዋን የቀመሰ እርሷን ሳያመሰግን መቦዘን የሚቻለው አንጀቱስ የሚችልለት ማን አለ?!
    + በስደቷ ጊዜም ሔዋን በሠራችው ሥራ መሰደብ የሚገባትን ስድብ ተሰድባለች፤ ሔዋን መጠማት የሚገባትን ጥማት፣ መራብ የሚገባትን ረሐብ፣ መጨነቅ የሚገባትን ጭንቀት፣ ማልቀስ የሚገባትን ልቅሶም ሁሉ በርሷ ተገብ'ታ ፈጽማለች።

ቤዛዊተ ዓለምና ሕማመ መስቀሉ

    + መስቀሉንም ስናስብ ወላዲተ አምላክን ነጥለን ማሰብ ከቶ እንዴት ይቻለናል? ከእግረ መስቀሉ እስኪደርሱ ድረስ ልጇ ከተያዘበት እለት አንስቶ የተጨነቀችውን ጭንቀት፣ ያዘነችውን ሐዘን፣ ያለቀሰችውን ልቅሶ ጥቂት ጊዜ ሰጥተን ብናስበው ያስጨንቃል። ርኅርኅተ ሕሊና እመብርሃን ልጇ ፍጹም ካሣን ሊክስ ወደ እዚህ ዓለም መጥቶ መከራን ሲቀበል በነገረ ድኅነት ውስጥ እንዴት ፍጹም ካሣን እንደካሰ ልብ በሉ።

     + ሔዋን ያጣችውን ድንግልና በድንግል እመቤታችን መለሰላት። ዳግሚት ሔዋን እመብርሃንን የድኅነተ ዓለም ሥራው ላይ እንዴት እንዳሳተፋት ልብ አድርጉ። ዓለሙ ሁሉ እርሱን ፈጣሬ ዓለማትን ለማስተናገድ እምቢኝ ባለበት ጊዜ፣ ዓለሙ እሺ በጄ ብሎ ቢፈቅድም እንኳ የነበረበት ዕዳ በደል እግዚአብሔርን ለመቀበል ያልበቃ በሆነበት ጊዜ በዓለሙ ሁሉ ፈንታ ራሷን ለልዑል ማደሪያነት የሰጠች፣ ንጽሕናዋም እግዚአብሔርን ማርኮ ከሰማይ ወደ ምድር እስኪያመጣው ድረስ ምዕዝት ሁና የተገኘች ከሷ በቀር ማን፡ነበር?!
      + ለይኩን ብርሃን ብሎ ዓለማትን በብርሃን ጎርፍ ብሩህ ያደረገው፡ፀሐየ ጽድቅን ይኩነኒ ብላ የፀነሰች ከርሷ በቀርስ፡ማን ነው?! ሉቃ፩

👉ሌላኛው ቤዛ ማለት ዋስ ጠበቃ ማለት እንደሆነ ተመልክተናል። "ወትቀውም ንግሥት በየማንከ" ያለው ልበ አምላክ ለምን ይሆን? ንግሥቲቱ በቀኙ የወርቅ መጎናጸፊያ ተጎናጽፋ የቆመች ምን ብላ ይሆን?
   + መቆም በቤተብክርስቲያናችን በብዙ መንገድ ይፈታል። ቆመ፡ብሎ ፈረደ፣ ቆመ ብሎ አማለደ ይላል። በዚህ ዐውድ ትቆማለች የተባለላት እመብርሃን ለምልጃ መሆኑን ልብ ይሏል። የዶኪማስን ቤት ስናስብ፣ በሠርጉ ላይ የወይን ጠጁ ባለቀ ጊዜ ርኅርኅተ ሕሊና ልጇን ወዳጇን የወይን ጠጅ 'ኮ የላቸውም ብላ ስትለምነው ልጇም "አንቺ ሴት ካንቺ ምናለ፥ ጊዜዬ ገና አልደረሰም" በማለት ሲመልስላት ሄዳ አስተናጋጆቹን "የሚላችሁን አድርጉ" አለቻቸው። ለምን ይሆን እንዲህ ያለቻቸው? ከልጇ ጋር ባይግባቡ ኑሮ እርሱም ባይቀበላት የሚላችሁን አድርጉ ልትል እንዴት ቻለች?! ዮሐ፪
   + የእናት ልመና ፊት አያስመልስ አንገት አያስቀልስ ይላሉ አበው። ምልጃዋን ልጇ ወዶ ፈቅዶ የሚቀበልላት የአምላክ እናት ወላዲተ አምላክ ቤዛዊተ ዓለም ናት። ለዚህም፡ነው እንዲያውም ማር ቅዱስ ያሬድ ሊቅ በሚያስደንቅ ቃል "ለኪ ይደሉ ከመ ትኩኒ መድኃኒቶሙ ለመሃይምናም ሕዝብኪ፥ ለምእመናን ወገኖችሽ መድኃኒታቸው ልትባይ ይገባሻል" አለ። ምክንያቱንም ሲነግረን "ወታስተሥርዪ ኃጢአተ ሕዝብኪ ተበውሃ ለኪ እም አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ - የሰው ልጆችን ኃጢአት ታስተሠርዪ ዘንድ ከአብ ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ ሥልጣን ተሰጦሻልና" በማለት ያስረዳናል። ስለዚህም ዘወትር ስንጸልይ "ሰአሊ ለነ ቅድስት፥ ወልድኪ ሣህሎ ይክፍለነ ሰአሊ ለነ ቅድስት" እያልን እንማጸናታለን።

እንግዲህ ልብ አድርጉ በመጽሐፍ ስንኳን ወላዲተ አምላክ ይቅርና ሀብት ንብረት ቤዛ ተብሎ የለ? ይህን ሁሉ የሆነችልን እመቤት፣ የሕይወትን ውሃ አፍልቃ ከጥም ያረካችን ምንጭን ቤዛዊተ ዓለም ማለት ታዲያ ምኑ ላይ ነው ጥፋቱ?!ወላዲተ አምላክን ቤዛዊተ ዓለም ስንል ያለምንም መሳቀቅና በድፍረት እጅግ ደስ እያለን የምንለው ለዚህ ብቻም አይደለም። ለበዓሉ ማዘከሪያ እንዲሆን ጥቂት ተናገርን እንጂ።

ቤዛዊተ ዓለም የተባልሽ እመብርሃን ከልጅሽ ከወዳጅሽ ይቅርታን ለምኝልን። አሜን።
ይቆየን!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር።

©ዘዲያቆን መልአኩ ይፍሩ ዘውሉደ ብርሃን
ኅዳር ፮፥ ፳፻ወ፲፩ ዓ.ም
ሲቹዋን ቸንዱ፣ ቻይና

ሰኞ 12 ኖቬምበር 2018

እግዚአብሔርን ተስፋ አድርግ

እግዚአብሔርን የምትወድ ነፍስ ረፍቷ በእግዚአብሔር እና በእግዚአብሔር ብቻ ነው። ሰዎች በዚህ ዓለም ውስጥ በሚጓዙበት መንገድ ሁሉ በእግዚአብሔር ተስፋ ወደ ማድረግ እስካልቀረቡ ድረስ ሰላም አይሆኑም።
                                  ቅዱስ ይስሐቅ ሶርያዊ
Photo:- Mark Sadek

እሑድ 11 ኖቬምበር 2018

🙏የጽድቅ ሥራ ከባድ ነውን?🙏

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

         (መልስ ከመጽሐፈ ገነተ አበው ቅዱሳን
          Paradise of the holy fathers )
/ትርጉም፥ ዲያቆን መልአኩ ይፍሩ/
+ + +                + + + +              + + +

    👉ተወዳጆቼ፣ ራሳችንን አንድ ጊዜ ላስገዛንለት ምግባር ቀናኢያን(zealous) እንሁንና ለመጓዝ በጀመርነው መንገድም ወደ ፍጻሜው (ለመድረስ) እንሂድ፤ እናም የሎጥን ሚስት ልንመስላት አይገባምና ከእኛ መኻከል ማንም ሰው በኋላው ያለውን (ወደ ኋላው) አይመልከት። /ዘፍ ፲፱፥፳፮/ የጽድቅን መንገድ ትምህርት ከተቀበለ በኋላ ወደ ኋላው ለሚመለስ ሰው፣ ወደ መንግሥተ ሰማያት መግባት ቀላል አይሆንለትም፤ ወደ ኋላው የሚመለሰው ያ ሰው የተመለሰው በምንም ዓይነት መንገድ ቢሆን፣ ባደረገው ነገር ይጸጸታል እናም ልክ ውሻ ወደ ትፋቱ እንዲመለስ ሁሉ እሱም ወደዚህ ዓለም ንብረቶች ይመለሳል።/ምሳ፳፮፥፪፤ ፪ጴጥ፪፥፳፪/ ደግሞም ሰማያዊ ሸክም ከባድ እንደሆነ (እያሰባችሁ) አትፍሩ፤ ለሚፈልጉት የጌታችን ሸክም ልዝብ እና ቀሊል ነውና።/ማቴ፲፩፥፴/ ስለዚህ መሻቱ ካለን ሁሉም ነገር ቀላል ነው።
     👉የዚህ ዓለም ልጆች፣ በትምህርቱ ምንም ዓይነት የቅድስና መንገድ የማይገኝበትን (የሌለበትን) እና በምስጋናውም ምንም ዓይነት የሕይወት ረብ ጥቅም የሌለበትን ርካሽ ጥበብ ይማሩ ዘንድ በባሕሩ ላይ ይጓዛሉ፤ ከባድ ወደ ሆኑ ሀገራትም ስንኳ ጉዞ ያደርጋሉ። ነገር ግን እኛ (እንደነርሱ) ስለመንግሥተ ሰማያት ብለን ጉዞ እንድናዘጋጅና በባሕር ላይም እንድንሄድ አልተፈለገብንም፤ ጌታችን አስቀድሞ እንዲህ ብሎ በመናገር አውጆልናልና። "መንገሥተ ሰማያት በመኻከላችሁ ናት" /ሉቃ ፲፯፥፳፩/ ስለዚህ ወዳጆቼ፣ ሕይወት በእኛ ውስጥ ነውና ያለችው ሕይወታችንን ማግኘትም በእጃችን ነው፤ የሚገለገለውም በራሳችን ነው። ነፍስ በባህርይዋ የለባዊነት ባለቤት ናትና ሕይወታችን ምን እንደሆነ ዕውቀቱ አላት፤ ይህም በአፈጣጠሩ ጠባይ ምክንያት ለወደደው (ለፈቀደው) ነገር ሁሉ (ዝንባሌ ያለው) ፍጹም የተዘጋጀ ነው። ስለዚህ የነዌ ልጅ ኢያሱ፣ ሕዝቡን እንዲህ በማለት አዘዘ"በእስራኤል አምላክ በእግዚአብሔር ፊት ልባችሁን አዘጋጁ" /ኢያ ፳፭፥፳፫/ እንዲሁም ዮሐንስ "መንገዱን አስተካክሉ" /ሉቃ፫፥፬/። አሁን መጽሐፉ ነፍስን ስለማዘጋጀት ሲደነግግም የመጀመሪያው ተፈጥሮአዊ ጠባይዋን በርሷ ውስጥ ጸንቶ እንዲቆይ ከመሻት ነው፤ ነገር ግን ከዚህ ወጥታ ልኳን አልፋ ብትሄድ ልክ እንደክፉው (እንደሰይጣን) የተለየች ውግዝት (የታመመች ድውይት የተፈረደባት ጊግይት) ትሆናለች። ስለዚህም ጉዳዩ ለእኛ ከባድ አይደለም።
ይቆየን።
+ + +               + + + +               + + +
የቅዱሳን አበው በረከት ይደርብን።

©ዘዲያቆን መልአኩ ዘውሉደ ብርሃን
ኅዳር፪/፳፻ወ፲፩ዓ.ም
ሲችዋን ቸንዱ/ ቻይና

ረቡዕ 7 ኖቬምበር 2018

❤️ የቅዱስ እንጦንስ እና የሰይጣን ቃለ ተዋስዖ ❤️

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

    + + +              + +  + +               + + +

ምንጭ፥ paradise of the holy fathers
               (መጽሐፈ ገነተ አበው ቅዱሳን)
ትርጉም፥ ዲያቆን መልአኩ ይፍሩ ዘውሉደ ብርሃን

❤️ . . . ዳግመኛም ጠላት በዚህ ትግል ድል እንደተደረገ እና ማታለሉም በጻድቁ ሰው ሐሳብ(ልቡና) እንደተናቀ እና እንደተወገደ ባየ ጊዜ፣ ጥርሱን አፋጨና ምናልባትም በማስፈራራትና በማስደንገጥ ፈቃዱን የሚፈጽምበት ዕድል አገኛለሁ በማለት ጮኸና ለጻድቁ ሰው ውሳጣዊ ክፋቱን በግልጥ አሳየው። በቅዱስ እንጦንስ ፊትም እንደ አንድ የህንድ(ጥቁር) ወንድ ልጅ ሁኖ ተገለጠና እንዲህ ይለው ጀመር "ማንን ታያለህ? መጥቻለሁ እናም እቆማለሁ፤ አንተንም አሸንፍህና ሌሎቹን እንዳደረግሁ አንተንም የተዋረድህ የወደቅህ አደርግሀለሁ"። እኒህን ቃላት እየተናገረምን ሳለ ንዑድ ክቡር የሆነ እንጦንስ በራሱ ላይ በትዕምርተ መስቀል ምልክት አማተበና ፍርሐቱን ተወ፤ ጠላትም የመስቀሉን ምልክት ዐይቶ ፈራ(ደነገጠ)። በዚህም ጊዜ ጻድቅ እንጦንስ (ሰይጣን) እንደፈራ ሲመለከት እንዲህ በማለት ይጠይቀው ጀመር "ማነህ አንተ እናም እንዲህ ያሉትን ቃላት በእኔ የሚሰ'ሙት በማን ድምጽ ነው?" ከዚያም ጠላት በሚዝት(በሚደነፋ) ሰው ዓይነት ኹኔታ እንዲህ ይለው ጀመር " እኔ፣ እኔ እንኳን ስሕተትንና ዝሙትን እወዳለሁ፤ እናም እኒያን (የሐሳብ) ውጊያዎችና ሽንገላዎች (ወደ ሰው ልጅ ልቡና) የማመጣ (የምጨምር) እኔ ነኝ። ብዙዎችን ወደ ስሕተት እንድወስድ (የምተጋ) እኔ ነኝ፤ እንዲሁም ማንኛውንም ሰው እዋጋለሁ፤ የጽድቅ ተቃዋሚ ነኝ። ነቢዩም እንኳ እንዳለው 'የዝሙት(የግልሙትና) መንፈስ'(ሆሴ፬፥፲፪) እኔ ነኝ፤ በእኔ የተደናቀፉ ሁሉ ወደ ስሕተት ገብተዋልና። ለብዙ ጊዜያት አንተንም የጎዳሁህ እኔ ነኝ፤ አንተም በሁሉም ነገር በእኔ ማዋረድ ተፈትነህ ነበር"

❤️   ብጹእ የሚሆን እንጦንስም እግዚአብሔርን አመስግኖ ታላቅ የሆነ ብርታት አገኘና እንዲህ አለ "ጠላቴ ሆይ የመስቀሉን ኃይል ለመቋቋም (የሚሆን) በአንተ ውስጥ ያለ እንደምን ዓይነት ኃይል አለና እንዲህ አሰብህ? በባህርይህም ጥቁር ነህና በቅጣትም እንደተ'ናነሰ ምስኪን ሕጻን ልጅ ደካማ ነህና እንዲህ ባለ'ው ሁኔታ በህንዳዊ (ጥቁር) ሕጻን ልጅ መልክዕ መገለጥህ ትክክል አድርገሃል። አንተ በእኔ ዘንድ እንደተናቀ ነህ፤ እናም በሽንገላዎችህ (በማስፈራራትህ) አልደነግጥም። ጌታዬም ረድቶኛልና በጠላቶቼ ላይ (በድል) እሰለጥንባቸዋለሁ"። ያም ጥቁን ነገር እሊህን ቃላት በሰማ ጊዜ፣ ከእንጦንስ ፊት ፈጥኖ ጠፋ። ይህም ቅዱስ እንጦንስ ከጠላቱ ጋር ያደረገው የመጀመሪያው ክርክር ነው። ይልቁንም ይህን እንጦንስ ለመርዳት፣ በሥጋው ኃጢአትን ድል ካደረገ እና የሕጉ ቅድስና በእኛ ውስጥ ይመ'ላ ዘንድ እንዲሁም ከመንፈስ በኋላ እንጂ ከሥጋ በኋላ እንዳንጓዝ ከአዳኛችን (ከቤዛችን) የተደረገ የመጀመሪያው ርዳታ ነው።(ሮሜ፰፥፬)
                        ይቆየን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር።

©ዘዲያቆን መልአኩ ዘውሉደ ብርሃን
ጥቅምት ፳፰/ ፳፻ወ፲፩ ዓ.ም
ሲቹዋን ቸንዱ/ ቻይና

ማክሰኞ 6 ኖቬምበር 2018

➕➕➕ በእንተ መድኃኔዓለም ➕➕➕

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

. . . ለምን ተገለጠ፧. . . ድኅነተ ዓለም ለምን በሞት?. . . ከሞትም የመስቀል ሞት ለምን? . . . ለምን እርሱ ሆነ?. .

በአብ ስም አምኜ አብን ወላዲ ብዪ፣ በወልድ ስም አምኜ ወልድን ተወላዲ ብዬ፣ በመንፈስ ቅዱስ አምኜ መንፈስ ቅዱስን ሠራጺ ብዬ አምኜ፣ ምንም ለአጠይቆ አካላት(አካላትን ለማሳየት) ሦስት የምል ብሆንም መለኮቱ የሚያገናዝበው፣ አንዱ በአንዱ ሕልው፡ሁኖ የሚኖር አንድ አምላክ ብዬ በማመን ነገረ መስቀሉን ለማዘከር መናገር እጀምራለሁ። ለእመ ረከብክሙ ቀለመ ዘተናገርኩ በዘኢይደሉ አንትሙ አርትዑ ወኅድጉ ሊተ- በማይገባ የተናገርሁት ቀለም ብታገኙ ይቅር ብላችሁኝ ታቀኑት ዘንድ እጠይቃለሁ።

ነገረ መስቀሉን፣ ሥግው ቃልን የመከራውን ነገር ባሰበ ጊዜ የማይመታ ሕሊና፣ የማይጨነቅ አእምሮ፣ የማይንቀጠቀጥ ብረክ ፈጽሞ አይገኝም። በለምለም መስክ የሚመራቸውን እና ወደ እረፍት ውሃ የሚወስዳውን መልካሙን እረኛቸውን በጎቹ ሲገድሉት አይታ ምድር እንኳን ጨንቋት ስትንቀጠቀጥ ያየ ዐይን፣ ዐለታት የአንተን ቅዱስ ደም እንዴት ልንሸከም ይቻለናል ብለው ሲሰነጣጠቁ፣ ፍጥረት ሁሉ አንድ ሁኖ በመስቀል ከፍ ብሎ ዕርቃኑን ሁኖ በግፍ የተሰቀለው በእውነት ፈጣሬ ዓለማት መፍቀሬ ሰብእ ሥግው ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን ሲመሰክሩ ተመልክቶስ የርሱን አምላክነት የማይረዳና እጹብ ድብንቅ በማለት ለዚህ መጠን ለማይደኝለት ድንቅ ፍቅር በማድነቅ ምስጋና የማያቀርብና የማይገ'ዛ ማን ነው?!

#ለምን ተገለጠ
  + መፍቀሬ የዋሂይ ርግብ ቅዱስ ሕርያቆስ በቅዳሴው "ፍቅር ሰሐቦ ለወልድ ኃያል እመንበሩ ወአብጽሖ እስከ ለሞት-ኃያል ወልድን ፍቅር ሳበው፤ እስከ ሞትም አደረሰው" በማለት በታላቅ ተመስጦ የሚነግረን ነገር ለዚህ ጥያቄ መልስ ነው። ኃያል አምላክን ማንም ማን #ሊመስለው እና በምንም በምን #ሊመሰል የማይቻል "ኅቡር ሕላዌሁ ነጽሮተ ገጹ ኪሩቤል (ምሉአነ አዕይንት) ኢይክሉ" የሚባልለት ድንቅ አምላክን እንደምስኪን ድሃ እንዲገለጥ ወደዚህ ታላቅ ትሕትና የሳበው ፍቅር ብቻ ነው። በዚያውም ላይ መፍቀሬ ሰብእ መድኃኔ ዓለም፣ ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚገልጥልን "የተጠማ ሰው ለመጠጣት እንዲቸኩል እግዚአብሔርም (ከመዓት ይልቅ) ለምሕረት ይቸኩላል"ና ነው።
  + በመጽሐፍ ሐዋርያ ሊያስብል በሚያስደፍር ሁኔታ ሐዲስ ኪዳን ላይ አብሮ በአካል ጌታችን ከዋለበት ውሎ ካደረበት አድሮ ከርሱ የተማረውን እንደሚመሠክር እንደአንዱ የጌታ ደቀመዝሙር፣ ስለሐዲስ ኪዳን በሚያስደንቅ መንገድ የሚነግረን ቅዱስ ኢሳይያስም "የሟቹን ሞት አልፈቅድም" ብሎ እንደተናገረ በመግለጥ ቸርነቱን ይነግረናል።
  + ሊቁ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ የደረሰልን መጽሐፈ አክሲማሮስም እንደሚነግረን በፍጥረት ሥርዓት ውስጥ ካሉት ከአሥራ ሁለቱ ነፋሳት ውስጥ የመዓት ነፋሳት የሚባሉት አራቱ ብቻ ናቸው። ይኸውም ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ እንዳለው "ርሑቀ መዐት ወብዙኃ ምሕረት" የሆነ መፍቀሬ ሰብእ አምላክ ነውና ስለዚህ ሊገለጥ ወደደ።
  + ከዚህ ላይ ጸረ አርዮሳውያን፣ የተዋሕዶ አርበኛ የሆነው ሊቁ ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ በነገረ ሥጋዌ ትምህርቱ የእኛ በመቅበዝበዝና በጨለማና በሞት ጥላ ውስጥ በክፋት ሠራዊት የማታለል ሥራ ውስጥ መኖርና አንድ ጊዜ አርአያ እግዚአብሔር የተሰጠን ሁነን ሳለን የዚህ ተካፋይ የሆን' እኛ ከፍጹም መጥፋት በፍጥነት እየተንደረድርን ሲያይ ይህን' ነገር ቸርነቱ ታግሳ ማየት ስላልቻለች ይህ መከራችን የሕያው ፍቊር አምላክን ፍቅሩን ጠራችው በማለት ይነግረናል። የተገለጠውም #ለድኅነተ ዓለም ነው እንጂ ለርሱ ምንም ምን ሊረባው አይደለም። አስቀድሞ ሰይጣን እንደኔ ያለ ድንቅ ፍጡር ስለማያገኝ ደግሞ ይመልሰኛል ብሎ በትዕቢት ቢናገር ማንም ማን ሊመስለው የማይቻል የአምላኩን አምሳል ገንዘብ ያደረገ ልዩ ፍጥረት ፈጠረ። ዳግመኛም አምላክ ትሆናለህ ብሎ ከክብር ቢያዋርደውም የሰይጣንን ተሳልቆ በራሱ በሰይጣን ላይ አደረገበትና ሥጋን አምላክ አደረገው። "ከመ ትንስቶ ለጸላኢ" እንዳለ ልበ አምላክ።

#ድኅነተ ዓለም በሞት ለምን?
+ ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ እንደሚነግረን፣ ሰው የተሰጠቸውን የጦም ሕግ በመሻሩ የመጣችበት ቅጣቱ በባሕርዩ የነበረችውን እና በርሱ ላይ ምንም ምን ስልጣን ያልነበራትን ሞትና ሙስና መቃብርን በርሱ ላይ እንድትሰለጥን ኃይልን አጎናጽፏታልና ይህ በንስሐ ብቻ የሚመለስ እንዳይደለ በጥልቀት ተንትኖ ያስረዳል። አዳም ሲፈጠር በመዋቲ እና በሕያው መኻከለኛ ሁኖ ነበር። ትእዛዙን ቢጠብቅና ቢታግሥ ኖሮ፣ ፍጹም ሕያውነትን ገንዘብ አድርጎ ሞትን ልክ እንደቀድሞው እንደሰለጠነባት ለዘለዓልም ሰልጥኖባት ይኖር ነበር። መቼም መች አታገኘውም ነበር። ነገር ግን በሠራው በደል የመጣበት ቅጣት ባህርያዊ ጉስቁልናን አምጥታበታለችና ይህች የጎሰቆለች ባህርዩ ወደ ቀደመ ክብሯ መመለስ ስላለባት ሞት አስፈለገ።
  + እግዚአብሔርም ፈታሔ በጽድቅ ኰናኔ በርትዕ ነውና የፈረደው ፍርዱም መፈጸም ስላለበት ሞት አስፈለገ።

#የመስቀል ሞት ለምን?
+ ይህን ለማስረዳት ከቅዱስ አትናቴዎስ ትምህርት በከፊል እንውሰድ።
  " . . . እርሱ አንገቱን የተቆረጠውን የዮሐንስን ዓይነት ሞት አልሞተም፤ እንደኢሳይያስም በመጋዝ አልተሰነጠቀም። ቤተክርስቲያንን ለሚከፋፍል ሁሉ ከዚህ በኋላ ምንም ዓይነት ምሕረት እንደሌለው ለማጠየቅ በሞቱ ጊዜ እንኳን አካሉን ሳይከፋፈል እንዳለ' ጠብቆታል።

✝️  . . . ክርስቲያን (ክርስቶስ) ለምን በመስቀል ሞት እንደተሰቃየ እና በሌላ መንገድ (ሞቱ) ለምን እንዳልሆነ ለማወቅ ቢፈልግ ይህንን እንመልስለታለን፥ ለእኛ የሚጠቅም(የሚበጅ) የሆነ ሌላ ምንም ምን ዓይነት መንገድ የለምና ጌታ ለእኛ ሲል በርግጥም እጅግ መልካም የሆነውን አንዱን ሞት ተቀበለ። በእኛ ላይ የወደቀውን ርግማን ሊሸከም መጣ፤ ታዲያ የተረገመውን ሞት በመቀበል ካልሆነ በቀር በሌላ መንገድ እንዴት "ርግማን"(ገላ 3፥13) ሊሆን ይችላል። እንዲሁም "በእንጨት የሚሰቀል ሁሉ የተረገመ ነው" (ገላ3፥13) ተብሎ ተጽፏልና ያ ሞት መስቀሉ(የመስቀል ሞት ነበር)።
✝️  ዳግመኛም የጌታ ሞት የሁሉም ቤዛ ነው፤ እናም "በመካከል ያለው የጥል ግድግዳ" (ኤፌ 2፥14) በርሱ ፈራረሰና የአሕዛብም መጠ'ራት ሆነ። ሰው እጆቹን ዘርግቶ ሊሞት የሚችለው በመስቀል ላይ ብቻ ነውና ካልተቸነከረ እንዴት ሊጠራን ይችላል? ዳግመኛም እዚህ ጋር የቀደሙ ሕዝቦቹን (እስራኤል ዘሥጋን) በአንዱ፣ አሕዛብን ደግሞ በሌላኛው እጆቹ ጠርቶ ሁለቱንም በርሱ አንድ ያደርጋቸው ዘንድ ነውና የእጆቹ መዘ'ርጋትና ሞቱን እንዴት የተመቸ(fitness) እንደሆነ እንረዳለን። ይህ ቢሆንም ቤዛ ስለሚሆን ስለሞቱ ሁኔታ አስቀድሞ "እኔም ከምድር ከፍ ያልሁ እንደሆነ ሁሉን ወደ እኔ እስባለሁ"(ዮሐ 12፥32) በማለት ራሱ ተናግሮ ነበር።

✝️   ዳግመኛም አየሩ፣ ከሰማይ ከወደቀ በኋላ የርሱን ዓመጽ(disobedience) ከሚጋሩት ክፉ መናፍስት ጋራ በመሆን ነፍሳትን ከእውነቱ ለመከልከልና እውነቱን ለመከተል የሚጠሩትንም (መንፈሳዊ) እድገታቸውን ለመግታት የሚደክመው የዘራችን ጠላት የሆነው የዲያብሎስ ግዛት (መነኻሪያ) ነበር። ሐዋርያውም ይህን ሲያመለክት ነበር ". . .በማይታዘዙትም ልጆች ላይ አሁን ለሚሠራው መንፈስ አለቃ እንደሆነው በአየር ላይ ሥልጣን እንዳለው አለቃ ፈቃድ.  . ."(ኤፌ 2፥2) በማለት የተናገረው። ነገር ግን ጌታ ዲያብሎስን ይጥለው ዘንድ እና ሐዋርያውም እንደተናገረው "በመጋረጃው ማለትም በሥጋው.  . ."(ዕብ 10፥20) ወደ ገነት (ወደ ሰማይ) የምንወጣበትን "መንገድ" ሠራልን። ይህ ደግሞ መደረግ ያለበት በሞት ነው፤ ታዲያ በአየር ላይ በሚሆን ሞት ይኸውም በመስቀል ላይ ካልሆነ በቀር እንዴት ባለ' ዓይነት ሞት ይህ ሊደረግ ይችላል?

✝️   ዳግመኛም ጌታ መከራ መቀበሉ እንዴት ትክክለኛ እና የተገባ እንደሆነ ተመልከቱ። ስለዚህም "ከመሬት ከፍ" በማለቱ ከጠላት ክፉ ጫናዎች ሁሉ አየሩን ንጹሕ አደረገው። "ሰይጣንን እንደመብረቅ ከሰማይ ሲወድቅ አየሁ"(ሉቃ 10፥18) አለ፤ እና ስለዚህም ዳግመኛ "አርኅዉ ኆሀተ መኳንንት፥ ወይትረኃዋ ኆሀት እለ እም ፍጥረት፥ ወይባእ ንጉሠ ስብሐት - እናንተ መኳንንቶች፣ ደጆቹን ክፈቱ፥ የዘለዓለም ደጆች ይከፈቱ፥ የክብርም ንጉሥ ይግባ"(መዝ 23(24)፥7) በማለት ወደገነት የሚወስደውን መንገድ ዳግም ከፈተልን። የሁሉም ጌታ ስለሆነ፥ የትኛዎቹም የርሱ ሥራዎች ሁሉ ለርሱ(ለሠሪያቸው) የተዘጉ አይደሉምና አካላዊ ቃል የደጆቹ መከፈት ለርሱ የሚያስፈልገው አይደለም። በፍጹም፤ ይህ ያስፈለገን በራሱ ሰውነት የተሸከመን እኛ ነን እንጂ። ይህንንም አስቀድሞ ስለሁሉ ፈንታ ለሞት አሳልፎ ሰጠውና ከዚያም በርሱው ወደገነት (ወደ ሰማይ) የሚወስደውን ጎዳና ሠራልን።" (St Athenasius on incarnation-Chapter 4)

#ይህን ለምን ሌሎቹ ማድረግ አልቻሉም?

+ ይህንንም ለማድረግ እና ደቂቀ አዳምን ከሞት ነጻ ለማድረግ፣ ፍጹም ሕያው የሆነ እና በሞት የማይሸነፍ አካል ያስፈልጋል። ስለዚህ ባለዕዳ ባለዕዳን ካለበት ብድር ዕዳ ነጻ ሊያደርገው እንደማይችል ሁሉ በዕዳ ውስጥ የነበሩት የኦሪት ካህናትና ነቢያት ደቂቀ አዳምን መታደግና ወደ ቀደመ ክብሩ መመለስ አልቻሉም።
+ ይህ የሚያድነው አካል ደግሞ መስዋዕት ለመሆን መሞትና መነሳት በዚህም ሞትን መግደል አለበት። መላእክት ደግሞ በባህርያቸው የማይሞቱ ናቸውና ስለዚህ መላእክት አልሆኑም። ይህም ብቻ ሳይሆን የበደለው የሰው ልጅ ስለሆነ ካሣ መክፈልም ያለበት የዚያ ወገን የሆነ ይኸው ሰው የሆነ ነውና ስለዚህ አዳኙ ሲገለጥ የሰውን ዕዳ የሚከፍል የሰው ወገን ዘመድ ሁኖ ሳለ ሕያው የሆነ ሞት የማያሸንፈው መሆን ይኖርበታል። ይህን ደግሞ መላእክት ማድረግ አይቻላቸውም።
+ ከሦስቱ ሕያዋን ፈጣሬ ዓለማት አጋእዝተ አለም ሥሉስ ቅዱስ ደግሞ ለምን እርሱ ተገለጠ ትለኝ እንደሆነ፣ አካላቸው ስማቸው ስማቸው ግብራቸው ነውና የአብ አካላዊ ግብሩ መውለድ ብቻ ስለሆነ ዘለአለም አብ ሲባል ይኖራል እንጂ ወልድ ወይም መንፈስ ቅዱስ ሊባል አይቻልም። የወልድም አካላዊ ግብሩ መወለድ ነውና በተለየ የአካል ግብር ስሙ ዘለዓለም ወልድ ሲባል ይኖራል እንጂ አብ ወይም መንፈስ ቅዱስ ሊባል አይቻልም። መንፈስ ቅዱስም በተለየው የአካል ግብር ስሙ መንፈስ ቅዱስ እንጂ አብን ወይም ወልድን ሊባል አይቻልም። ስለዚህም ከአብ አብን አህሎና መስሎ ከርሱ የተገኘው ወልድ ከአብ ተለይቶ የኖረበት ጊዜ የለም። ስለዚህ አብ ወልድን በመውለዱ በአካል ግብር ስሙ አብ ሲባል ይኖራል። ወልድም ከአብ ያለመቀዳደም በመገኘቱ ዘለዓለም ወልድ ሲባል ይኖራል። ስለዚህም በማኅፀነ ማርያም ሊያድርና ሊወለድ የሚገባው አካላዊ ቃል ወልድ ነው። እርሱ ሲወለድ ሥላሴ በፈቃድ አንድ ናቸውና በሦስቱም ፈቃድ ነው። #ድኅነተ ዓለም #ሥምረተ ሥላሴ ፈቃደ ሥላሴ ናትና። ይህቺ ሥምረተ ሥላሴ ግን በግብር የተፈጸመበት መወለድ ግብሩ የሆነው አካላዊ ቃል ወልደ እግዚአብሔር ነው።
  + እንግዲያማ ይህ በተለየ አካሉ ለድኅነተ ዓለም ለኩነተ ሥጋ የተገለጠው ወልደ እግዚአብሔር እግዚአብሔር ነዋ።
ይህ ገርሞት ደንቆትኮ ነው ማር ሶርያዊ ቅዱስ ኤፍሬም "ንዑ ርእዩ ዘንተ መንክረ፤ ወዘምሮ ዘምሩ በእንተ ምሥጢር ዘተከሥተ ለነ እስመ ዘኢይሰባእ ተሰብአ ቃል ተደመረ ወዘአልቦ ጥንት ኮነ ቅድመ ወለዘአልቦቱ መዋዕል ኮነ ሎቱ መዋዕል - ኑ ይህን ድንቅ ተመልከቱ፤ ሰው ያልሆነ እርሱ ሰው ሁኗል ቃል ተዋሕዷልእና ጥንተ የሌለው (ሥጋ አዳም) ከቀድሞ ጀምሮ የኖረ ተባለ ዘመን የማይቆጠርለት (መለኮት) ዘመን የሚቆጠርለት ሆኗልና ስለዚህ ድንቅ ምስጢር መዘምርን ዘምሩ" በማለት ያመሰግናል።

ኦ መድኃኒታችን ስላፈሰስኸው ደምህ፣ ስለአማኑኤል ስምህ፣ ስለድንግል ርኅርኅተ ሕሊና የዋሂት ርግብ እናት ስለጻድቃን ቅዱሳን ወዳጆችህ ብለን በኃጢአት የተዳደፍን እኛ በደለኛ ልጆችህን እንደቸርነትህ ብዛት ማረን ይቅድ በለን። አሜን በእውነት ያለሐሰት ይሁን ይደረግልን።
ይቆየን።
©ዘዲያቆን መልአኩ ዘውሉደ ብርሃን
ጥቅምት ፳፯-፳፻ወ፲፩ ዓ.ም
ሲቹዋን ቸንዱ/ ቻይና