በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።
ትርጉም፦ ዲያቆን መልአኩ ይፍሩ ዘውሉደ ብርሃን)
ውድ የኾናችሁ የእግዚአብሔር ልጆች እንደምን አላችሁ? እንኳን እመቤታችን በስደቷ እለት ያረፈችበትን
ደብረ ቊስቋምን ለምናስታውስበት ክብረ በዓል አደረሳችሁ። የቅዱስ ቆጵረስን እና የቅዱስ ፔታርፔሞቲስን ተጋድሎ ካቆምንበት እንቀጥላለን።
በዛሬው ክፍል የኹለቱን ቅዱሳን ተጋድሎ የመጨረሻውን ክፍል ከነቅዱስ አትናቴዎስ ጋር ኹነን እንመለከታለን። የቅዱሳኑ ኹሉ ጸሎት
እና የእግዚአብሔር ቸርነት የእናት ዓለም አማላጅነት አይለየን። አሜን።
ዳግመኛም ብዙ
ወንድሞች በዚያ ተሰብስበው ሳለ ጌታችን ለእኛ ያዘጋጀልንን አንድ ድንቅ ነገር ነገርን። እንዲህም አለ” በአንድ ወቅት ወደ ከተማ ኼድሁ፤ በዚያም አንድ
ማኒያዊ1(የማኒን መንገድ የሚከተል ሰው)ብዙዎችን ወደ ስሕተት እየመራቸው አገኘሁ። በዚያም ኹሉ ፊት
በግልጥ እየተቸሁ (እየተከራከርሁ)አሳምነው ዘንድ አልቻልሁም ነበርና(ኹኔታው ስላልተመቸ)፣ወደተሰበሰቡት ኹሉ ዞሬ እንዲህ አልሁ ‘ታላቅ እሳት አቀጣጥሉ፤ እናም
ኹለታችን (ያ እሳት)እንደዚያ እየነደደ ሳለ ወደርሱ እንግባ።በዚያ እሳትውስጥ ምንም ሳይቃጠል የቆየውም ሰው እውነተኛውን ሃይማኖት ይዟል።’ ታዲያም
ይህ ኹሉ ሲሆን፣ በዚያ የተሰበሰበውም ኹሉ በታላቅ ኹኔታ እሳቱን አቀጣጠለ። እኔም (ያነን)ማኒያዊ ከእኔ ጋር ወደዚያ እንዲገባ ጠየቅሁት። እርሱ ግን ‘እያንዳንዳችን በየራሳችን እንግባ፤ በዚያውም
ላይ ይኽ እንዲደረግ ያዘዝኸው አንተ ስለኾንህ አንተ ቀድመህ መግባት አለብህ’ አለ። ከዚያም በኢየሱስ ክርስቶስ ስም በላዬ ላይ በትእምርተ
መስቀል ምልክት እያሳየሁ ወደስሳቱ ገባሁ። በዚያም አልተጎዳሁም ነበር። እሳቱ (በተአምር)ወደጎን እና ወደጎን ተከፍሎ ነበርና አላስደነገጠኝም ነበር። እኔም በዚያ በእሳቱ
ውስጥ ለግማሽ ሠዓት ያህል ከቆየሁ በኋላ ሕኧቡ ኹሉ ይኽን ድንቅ ነገር ተመልክተው እየጮኹ አለቀሱ፤ እግዚአብሔርንም አመሰገኑ።(ልብ በሉተወዳጆ ች፣ ያላመነን ወደ እምነት ለማምጣት መጻሕፍትን ጠንቅቆ ማወቅ አይጠበቅብንም። ጌታችን ሥራችሁን አይተው
በሰማያት ያለውን አምላካችሁን እንዲያመሰግኑ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ኹሉ ፊት ይብራ እንዳለውእምነትን በሥራ በመግለት ብዙዎቹን ወደሃይማኖት መጥራት ይቻላል። ሰማእታት እንደሚያደርጉት
ማለት ነው።)ከዚያም ያን ማኒያዊ ወደእሳቱ እንዲገባ ነገሩት። ከፍርሐቱ የተነሳም ወደዚያ መግባትን እምቢ ባለ ጊዜ ሕዝቡ ኹሉ ያዙትና ወደ እሳቱ ጣሉት፤ እርሱም በመላ በእሳቱ
ተቃጠለ።እኔንም ያዙኝና በቤተ ክርስቲያን ላይ (ምራን)ብለው ሾሙኝ።ከዚያም ከኼዱ በኋላ እግዚአብሔርን አመሰገንሁ።“
”በአንድ ወቅትም
በአንድ የአሕዛብ የጥዖት ቤት እያለፍሁ ሳለ፣ አሕዛቡ ለጣዖቶቻቸው መሥዋዕት እየሠዉ ነበር። እኔም ‘እናንተ ማስተዋል
ያላችሁ ፍጡራን ኹናችሁ ሳለ ለማይናገሩ ነገሮች መሥዋዕት መሠዋታችሁ ስለምን
ነው?እናንተ ለማይናገሩ (ለጣዖታት)በመሠዋት በፈቃዳችሁ ዲዳዎች ኾናችሁን?’ አልኋቸው። እነርሱም የተናገርሁት ነገር መልካም እንደኾነ አመኑ፤
ተከትለውኝ መጥተውም በክርስቶስ አመኑ።“
“በዚያውም ላይ፣
ከአቅራቢያ መንደር አንድ ድኻ ሰው ይሠራበት የነበረ ከርቀት ወደእኛ ለሚሚመጡ ወንድሞች ደስታ (ታስቦ)የተዘጋጀ የአትክልት ቦታ ነበረን። ከአሕዛብም አንዱ ወደዚያ የአትክልት ቦታ ገብቶ
ጥቂት አትክልት ሰረቀና ከዚያ ቦታ ጠፋ። ነገር ግን ሊያበስላቸው አልቻለም ነበር። ከድስቱ በታች ለሦስት ሰዓታት ያህል እሳቱን
ቢያነድም እንኳ አትክልቱ ልክ ከአትክልት ሥፍራው ሲወሰዱ በነበሩበት ኹኔታ ቆዩ። ውሃውም እንኳን አልፈላም (ሊፈላ አልቻለም)ነበር። ያም ሰው ወደ ልቡ ከተመለሰ በኋላ(ይህን በማየቱ ደንግጦ ነበርና)የወሰዳቸውን አትክልቶች ይዞ ወደእኛ አምጥቶ ሰጠን። ከዚያም
ለዚህ ሥራው ይቅርታን ያገኝ ዘንድና ክርስቲያንም እንዲኾን ጠየቀን። ከዚያም በርግጥ ከእኛ ጋር እንደአንዳችን ኾነ። በዚያውም እለት ወንድሞች ከርቀት (እኛን ለማየት)መጥተው ነበር። እነዚያንም አትክልቶች ለነርሱ እናቀርባቸው እና ይደሰቱ ዘንድ ይገባ
ነበር። በቀመስናቸውም ጊዜ ጌታችንን አመሰገን። በኹለት ወገን ደስታን አግኝተናልና። የመጀመሪያው፣እኒህን አትክልት ሠርቆ የነበረው
ሰው ነፍስ በመመለሷ ሁለተኛው ደግሞ ወደእኛ የመጡት ወንድሞች በአትክልቶቹ ስለተደሰቱ ነው።”
ቅዱሱ አባታችን
ቆጵረስ እሊህን እና ሌሎችንም ብዙ ድንቅ ነገሮች ነገረን። እረፍት ካሳረፈንም በኋላ ወደ አትክልት ሥፍራው ወሰደንና በእግዚአብሔር
ለሚያምኑ ይህ በረሐ ፍሬን ሊሰጥ እንደሚችል ለነገራቸው ለነዚያ በክርስቶስ ላመኑ አባ ወራዎች መነሳሳትን እንዲፈጥርላቸው(አይተው እነርሱም በእምነት እንዲያደርጉ) በራሱ እጅ የተከላቸውን ቴምር እና ፍራፍሬዎችን አሳየን።
“እናም” አለ(ቆጵረስ)“አሽዋን ዘርተው ሰብሎቻቸው ሲበዙላቸው አይቻለሁ። እኔም ይኽን የአትክልት ቦታ ለወንድሞች ደስታ(ወንድሞች ይደሰቱበት ብዬ)ተከልሁ። ከዚያም አሁን ያለበትን ደረጃ ያዘ።(ብዛቱን እና እድገቱን ሲነግረው ነው)”
ተፈጸመ ፍካሬ ገድለ ቅዱስ ቆጵረስ ወቅዱስ ፔታርፔሞቲስ በሰላመ እግዚአብሔር።
ቅዱስ አትናቴዎስ ስለኹለቱ ቅዱሳን የጀመረውን ትረካውን ከዚህ ፈጽሟል። የቅዱሳኑ
ገድል ግን ቀጥሏል።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር። አሜን። ይቆየን።
©ዘዲያቆን መልአኩ ይፍሩ
ሕዳር 6/ 2010 ዓ.ም
ጎንደር/
ኢትዮጵያ
ምንም አስተያየቶች የሉም:
አስተያየት ይለጥፉ