ሐሙስ 21 ሴፕቴምበር 2017

የእሥራ ምእት ወአሠርቱ ዓ.ም በዓላት ወአጽዋማት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ
አሜን።
ውድ ወዳጆቼ እንኳን ለ2010 ዓ.ም በሰላም አደረሳችሁ። የባሕረ ሐሳብ ትምህርቱን በተከታታይ ለመጦመር የተቻለኝን ጥረት አደርጋለሁ።
የእሥራ ምእት ወአሠርቱ ዓ.ም ዘመነ ማርቆስ በዓላትና አጽዋማት
1/ ዓመተ ዓለም ማለት የዓለም እድሜ ማለት ነው።
ዓ.ዓ(ዓመተ ዓለም)= ዓመተ ፍዳ + ዓመተ ምሕረት
=5500+2010
=7510 ይሆናል።
2/ ወንጌላዊ ፥ ይህ ቀመር ዓመቱን የሚመግበውን ወንጌላዊ የምናውቅበት ነው።ይህም ከላይ ደምረን ያገግኘነውን ዓመተ ዓለም በ4 መግደፍ(4 እያደረጉ መመደብ) ከዚህም የሚቀረው ቀሪ ወንጌላዊ ይሆናል።
7510/4=1877 ቀሪ 2
ይህ የተገኘው ቀሪ
1 ቢሆን ማቴዎስ ይሆናል
2 ቢሆን ማርቆስ ይሆናል
3 ቢሆን ሉቃስ ይሆናል
0 (ያለቀሪ ቢካፈል ደግሞ) ዮሐንስ ይሆናል

ስለዚህ የ2010 ዓ.ም መጋቢ ወንጌላዊ ማርቆስ ነው ማለት ነው። እዚህ ቀመር ላይ ተካፍላ የተገኘችው ድርሻ መጠነ ራብዕት ትባላለች። ለዐራት ተካፍላ የተገኘች ድርሻ እንደማለት ነው። እርሷም ከዓመተ ዓለም ጋር ተጨምራ እለተ ዮሐንስን ለማስገኘት የምታገለግል ናት።

3/ እለተ ዮሐንስ፥ ይህ ቀመር መስከረም መች እንደሚብት(እንደሚገባ) የሚነግረን ነው። ይህም የሚሰ'ላው መጠነ ራብዕትን እና ዓመተ ዓለምን ደምረው በ7 መግደፍ ከዚያም ቀሪውን መውሰድ ነው።
=7510+1877
=9389 ይህን በ7 ቢገድፉት 1341 ቀሪ 0 ይሆናል።
ቀሪው 0 ቢሆን ሰኑይ
1 " ሠሉስ
2 " ረቡዕ
3 " ሐሙስ
4 " ዓርብ
5 " ቀዳሚት
6 " እሑድ ይሆናል። ቁጥሩም ከሠሉስ 1 ብሎ መጀመሩ በእኛ አቆጣጠር ጥንተ ቀመርን(የቁጥር መጀመሪያ) ሠሉስን ስለምናደርግ ነው ። ስለዚህ የ2010 መስከረም ወር የሚብተው ሰኑይ እለት ነው።

4/ ወንበር፥ መጥቅዕ እና አበቅቴ የሚባሉትን አስልተን ለማግኘት የምንጠቀምበት ቀመር ነው። ይህም የሚገኘው ዓመተ ዓለምን በ19 በመግደፍ ከዚያም ከሚገኘው ቀሪ ላይ "አሐደ አእትት ለዘመን- አንዱን ለዘመኑ ስጠው" በሚለው አዋጅ መሠረት አንድ ስንቀንስ ወንበርን
እናገኛለን።
7510 በ19 ቢገደፍ 395 ቀሪ 5 ይሆናል። ከቀሪው 1 ስንቀንስ 4 ይገኛል። በ2010 ዓ.ም 4 ወንበር ወጣ ማለት ነው።

5/ አበቅቴ፥ ይሄ ቀመር ደግሞ ከሕጸጽ ጋር እየተደመረ ሌሊትን የሚያስገኝ ነው። ስሌቱም
ወንበር× በጥንተ አበቅቴ(11) ከዚህ በኋላ በ30 መግደፍ ከዚያም የሚገኘውን ውጤት ቀሪውን ውሰድ።
= 4×11
= 44 ይህን በ30 ግደፍ። 1 ደርሶ 14 ይቀራል።
ስለዚህም በ2010 ዓ.ም 14 አበቅቴ ወጣ።

አዋጅ ፡
  አበቅቴ እና መጥቅዕ ሁልጊዜም ተደምረው 30
ነው የሚሆኑት።

6/ መጥቅዕ፡ ትርጉሙ ደወል ማለት ነው። ደወል ሲደወል ምዕመናን ካህናት ለጸሎት እንዲሰበሰቡ ሁሉ መጥቅዕም
በዓላቱን ሁሉ ይሰበስባቸዋልና ነው።
ስሌቱም
ወንበር× በጥንተ መጥቅዕ(19) ከዚህ በኋላ በ30 መግደፍ ከዚያም የሚገኘውን ውጤት ቀሪውን ውሰድ።
= 4×19
= 76 ይህን በ30 ግደፍ። 2 ደርሶ 16 ይቀራል። ስለዚህም በ2010 ዓ.ም 16 መጥቅዕ ወጣ።

አዋጅ፥
መጥቅዕ ከ14 በላይ ከሆነ ብዓለ ምጥቅዕ በመስከረም ይውላል፥ መጥቅዕ ከ14 በታች ቢሆን በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት ይውላል።
የ2010 ዓ.ም መጥቅዕም በምን እለት እንደሚውል ለማወቅ ከእለተ ዮሐንስ አንስተን መቁጠር ነው። መጥቅዕ 16 ስለሆነ በዓለ መጥቅዑ ጥቅምት ወርኅ ላይ ይውላል።
"መጥቅዕ ከ14 ቢበዛ በመስከረም ንዛ መጥቅዕ ከ14 ቢያንስ ከጥቅምት ዳብስ" እንዲል መስከረም የባተው ሰኑይ ስለሆነ ሰኑይ ለሰኑይ 8፡ ሰኑይ
ለሰኑይ 15 ይሆናል። ሠሉስ 16 ይሆናል። ስለዚህ በዓለ መጥቅዕ ሠሉስ እለት ይውላል። ይህንም ማወቃችን በዓላትን እና አጽዋማትን ለማወቅ የምትረዳንን መባጃ ሐመርን ለማግኘት ይህ ቀመር ስለሚያስፈልገን ነው።

7/ መባጃ ሐመር፥ ቃልነቱ ግእዝ ወይም ሌላ አይደለም። ፍርንዱስ ነው። ይህም ማለት የአማርኛ እና የግእዝ ቃላት ጥምረት ውጤት ነው ማለት ነው። መባጃ 'ባጀ፤ ከረመ' ካለው የአማርኛ ቃል የተገኘ ሲሆን ማክረሚያ ማለት ነው። 'ሐመር' ማለት ደግሞ በግእዝ መርከብ ማለት ነው። ስለዚህም በአጠቃላይ ትርጉሙ ማክረሚያ መርከብ ማለት ነው። ስሌቱም እንደሚከተለው ነው።

መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋለበት እለት ተውሣክ
ከዚያም የተገኘውን ውጤት በ30 በመግደፍ ቀሪውን መውሰድ። በዓላት እና አጽዋማት የሚውሉበትን እለት ለማወቅ ከበዓላቱ እና ከአጽዋማቱ ተውሳክ ጋር መባጃ ሐመርን በመደመር ከ30 ቢበልጥ በ30 ግደፍ። የቀረውንም ውሰድ። ነነዌ ግን በደረቅ መባጃ ሐመር ትወጣለች።

ትውሣክ፥
ማለት ጭማሪ ማለት ነው። ሁለት ዓይነት ተውሣካትን እንመለከታለን።
የእለታት ተውሳክ፥
ይህ ከቅዳሜ አንስቶ እስከ አርብ የሚቆጠር ሲሆን ቅዳሜን 8 ብሎ ዝቅ እያለ ይቆጥር እና ዐርብ ላይ 2 ይሆናል።
ቀዳሚት 8
እሑድ 7
ሰኑይ 6
ሠሉስ 5
ረቡዕ 4
ሐሙስ 3
አርብ 2 ይሆናል።
ስለዚህም በዓለ መጥቅዕ የዋለው ሐሙስ ስለሆነ ተውሳኩ 3 ይሆናል።

የ2010 ዓ.ም መባጃ ሐመሩንም ስናሰላ
መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋለበት እለት ተውሣክ፣ ከዚህ የተገኘውም ከሠላሳ ቢተርፍ በ30 ገድፈህ ቀሪውን ውሰድ። የበዓለ መጥቅዕም ተውሳክ፣ ሠሉስ እለት ስለሆነ ተውሳኩ 5 ነው።
16 + 5= 21 ይህም ከ30 ያነሰ ስለሆነ እንዳለው እንወስደዋለን። ስለዚህም በ2010 ዓ.ም 19 መባጃ ሐመር ወጣ።
አዋጅ፤
    1/ በዓለ መጥቅዕ በመስከረም ከዋለ ነነዌ በጥር ትውላለች።
    2/ በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት ከዋለ ነነዌ በየካቲት ትውላለች።
    3/ በዓለ መጥቅዕ በመስከረም ውሎ የእለት ተውሳክ እና
መጥቅዕ ሲደመሩ ከ30 ቢተርፍ በ30 ይገደፍና ነነዌ በየካቲት ትውላለች። የበዓላት እና የአጽዋማት ተውሣክ
ነነዌ 0
ዐቢይ ጾም 14
ደብረ ዘይት 11
ሆሳዕና 2
ስቅለት 7
ትንሣኤ 9
ርክበ ካህናት 3
ዕርገት 18
ጰራቅሊጦስ 28
ጾመ ሐዋርያት 29
ጾመ ድኅነት 1

8/ ነነዌ፡ በደረቅ መባጃ ሐመር የምትወጣ ተውሳክ የሌላት ናት። ስለዚህም በ2010 ዓ.ም ነነዌ በጥር 19 ትውላለች ማለት ነው። ከዚህ በታች የቀሩትን በዓላት እና አጽዋማት ለማግኘት ተውሣኩን ከመባጃ ሐመር ጋር መደመር የሚገኘውን ውጤት ከ30 ቢተርፍ በ30 ገድፎ ቀሪውን ወስዶ በቀጣዩ ወርኅ ማዋል ነው። ቀድሞት ከነበረው በዓልም ያነሰ ድምር ከተኘ በቀጣዩ ወር ይውላል።

10/ ዐቢይ ጾም፥
= 21+ 14
= 35 ይህን በ30 ቢገድፉት 1 ደርሶ 5 ይቀራል።
ስለዚህም የ2010 ዓ.ም ዐቢይ ጾም የካቲት 5 ይገባል ማለት ነው።

11/ ደብረ ዘይት፥
= 21+ 11
= 32 ይህንም በ30 ቢገድፉት 1 ደርሶ 2 ይቀራል።
ስለዚህም የ2010 ዓ.ም ደብረ ዘይት መጋቢት 2 ይገባል ማለት ነው።

12/ ሆሳዕና፥
=21 + 2
= 23 ስለዚህ የ2010 ዓ.ም ሆሳዕና መጋቢት 23 ይውላል ማለት ነው።

13/ ስቅለት፥
= 21 + 7
= 28 ስለዚህ የ2010 ዓ.ም ስቅለት መጋቢት 28 ይውላል ማለት ነው።

14/ ትንሳኤ፥
= 21 + 9
= 30 ስለዚህ የ2010 ዓ.ም ትንሳኤ መጋቢት 30 ይውላል ማለት ነው።

15/ ርክበ ካህናት፥ ይህ በዓል ደግሞ ኤጲስ ቆጶሳት
ለቤተክርስቲያን ጉሳይ የሚሰበሰቡበት ነው።
= 21 + 3
= 24 ስለዚህ የ2010 ዓ.ም ርክበ ካህናት ሚያዝያ 24 ይውላል ማለት ነው።
16/ ዕርገት፥
= 21 + 18
= 39 ይህን በ30 ቢገድፉት 1 ጊዜ ደርሶ 9 ይቀራል። ስለዚህ የ2010 ዓ.ም ዕርገት ግንቦት 9 ይውላል ማለት ነው።

17/ ጰራቅሊጦስ፥
= 21 + 28
=29 ይህን በ30 ቢገድፉት 1 ጊዜ ደርሶ 19 ይቀራል።
ስለዚህ የ2010 ዓ.ም ጰራቅሊጦስ ግንቦት 19 ይውላል ማለት ነው።

18/ ጾመ ሐዋርያት፥
= 21 + 29
= 50 ይህን በ30 ቢገድፉት 1 ጊዜ ደርሶ 20 ይቀራል። ስለዚህ የ2010 ዓ.ም ጾመሐዋርያት ግንቦት 20 ይውላል ማለት ነው።

19/ ጾመ ድኅነት(የዐርብ ረቡዕ ጾም)፥
= 21 + 1
= 22 ስለዚህ የ2010 ዓ.ም ጾመ ድኅነት ግንቦት 22 ይውላል ማለት ነው።
የ2010 ዓ.ም ባሕረ ሐሳብ ደረሰ ተፈጸመ በሰላመ እግዚአብሔር አሜን።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር አሜን።
©ዘዲያቆን መልአኩ ይፍሩ
አዲስ አበባ/ ኢትዮጵያ
መስከረም 1/ 2010 ዓ.ም

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ