ረቡዕ 27 ዲሴምበር 2017

“ ደቀ መዝሙርነት ”(ክፍል ሦስት)



በስመ ወወልድ ንፈስ ቅዱስ አዱ አላክ ን።

(በዲ መል ይፍሩ ውሉደ ርሃ)

በቀደመው ክፍል ላይ ደቀ መዝሙር የመምህሩንና የቀደሙትን ርቱዓን ደቀ መዛሙርት አሠረ ፍኖት መከተልና እነርሱን መምሰል እንዳለበት፣ በዚህም ስር ሌሎችን ነገሮችን አንስተን ተመልክተን ነበር። ለዛሬ ደግሞ የቀሩትን እንመለከታለን። ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን።
እውነተኛ ደቀ መዝሙር፦
v  ከመምህሩ ጎዳና የሚያስወጡትን ድምጾች ኹሉ ከመስማት ዠሮውን መዝጋት አለበት
o   ደቀ መዝሙር በመምህሩ ጎዳና ጸንቶ ተጉዞ ሽልማቱን ለመቀበል፣ ከመምህሩ ጎዳና አስወጥተው የሚያስጉዙትን ማናቸውንም ድምጾች መስማትን መተው አለበት። በመልካም ጎዳና እየተጓዘ  እስካለ ድረስ ደቀ መዝሙር ምንጊዜም ቢኾን የመልካም ነገር ጠላት የኾኑት ኹሉ እርሱን ለማስወጣት እንደተጉ መኾናቸውን ማስተዋል አለበት። በመጽሐፍ እንደተባለ “መንፈስን ኹሉ አትመኑ”፣ መንፈሳት ቅዱትን መስለው ርኩሳት መናፍስት ሊመጡ ይችላሉ እና በማስተዋል ሊጓዝ ይገባል።
o   ቅዱስ ዳዊትም በመዝሙሩ እንደተናገረው “ብጹእ ብእሲ ዘኢሖረ በምክረ ረሲዓን_ በክፉዎስ ምክር ያልኼደ ምስጉን ነው” እንዳለው ደቀ መዝሙርነቱ በትጋት ከመልካም ዋጋ ጋር ለመፈጸም ማስተዋል ይገባዋል። “ክፉ ባልንጀርነት መልካሙን ጠባይ ያጠፋዋልና ከማያምኑ ጋር በማይመች አካኼድ አትኺድ”። መጽሐፉ በማይመች አካኼድ አትኺድ አለ እንጂ ከማያምኑ ጋር ፍጹም አትገናኝ አላለም። በማይመች አካኼድ ማለት ምን ማለት ነው?
§  የሚያስተምሩንን ክኽደት እና ኢክርስቲያናዊ ጠባይ መቀበል
§  ወደሚያመልኩበት ቦታ አብሮ ኼዶ መሳተፍ
§  በምን ችግር አለው የሚነግሩንን ትንሽ የሚመስል ምግባረ  ሃይማኖት መተው(ምሳሌ፦ ጾምን መተው፣ የኢአማንያንን የአምልኮ ሥርዓት መሳተፍ፣ጸሎትን ከመጭራሹ መተው፣ ኢክርስትያናዊ ጸያፍ ትእይንቶችን መሳተፍ) እና የመሰሉትን ማድረግ የማይመች ተብለው በቅዱስ መጽሐፍ የተገለጡ ናቸው።
o   በዚህ አካኼዱ ላይ ደቀ መዝሙር መጠንቀቅ ካልቻለ በሰይጣን ወጥመድ እንደ ቅዱስ ሙሴ ባሕታዊ ተይዞ ይወድቃልና ሊጠነቀቅ ይገባዋል።
§  ቅዱስ ሙሴ ባሕታዊ ከመምህሩ ጋር ሲኖር መምህሩ ኹልጊዜም በበረሐ ስለሚኖሩት አበው ክብር እና ተጋድሎ ይነግሩት ስለነበር ልቡ በበረሐው ሕይወት ተመስጦ ነበርና እርሳቸው ካረፉ በኋላ ከዚያ ወደበረሐ ወጣ። በዚያም ለብዙ ዓመታት ከኖረ በኋላ አሸናፊነት ስሜት ሲሰማው ሰይጣን ከቀደሙት አበው አንዱን ተመስሎ በርቀት ከሙሴ በአት እየራቀ ይኼዳል። ሙሴም ይኽን ሲመለከት፣ በልቡ ማሰብ ይጀምራል ሰይጣንም ቀስእያለ በሙሰ ልብ ውስጥ ሐሳብ መፈጠሩን ስለተመለከተ ተጠግቶ አጠገቡ ይቀመጣል። ነገር ግን አያናግረውም ነበር። ልክ ሙሴ ለጸሎት ሲቆም ትቶት ይኼዳል፣ ሲጨርስ ደግሞ መጥቶ አጠገቡ ይቀመጣል፤ ግን አያናግረውም ነበር። ሙሴ መጠርጠር ቢኖርበትም እርሱ ግን ያሰበው “እኔ ከቀደሙ አባቶች ጋር ጸሎት ማድረግ የተገባኝ ባልኾን ነው”ብሎ ነበር።
§  ሰይጣንም በሙሴ ልብ ውስጥ ሐሳብ መግባቱን ከተመለከተ በኋላ ማናገር ጀመረው። ታሪኩን ነገረው እንዴት ካለ የዝሙት ኃጢአት እግዚአብሔር አውጥቶ ከዚህ ክብር እንዳደረሰው። እንዴት ያለ ሀብታም እንደኾነ እና ዛሬም የመጣው እረፍቱ ስለደረሰ ሙሴ እንደሚቀብረው ተነግሮት እንደኾነ ነገረው። ሙሴም በሙሉ ልቡ አመነው።
§  በበነጋው ተያይዘው ወደዚያ አባት (ሰይጣን) መኖሪያ በአት ተጓዙ። ከብዙ ድካም በኋላ ከአንድ ቤተመንግስት ከመሰለ ቤት ደረሱ። ያም ሰው ሙሴን “እንግዲህ ቤቴ ይኼ ነው። እንደምታየው እንደነገርኹህም ሀብታም ነኝ፤ አንተም የምትቀብረኝ በዚሁ ቦታ ነው። ” ይለውና አብረው ወደ ውስጥ ሲገቡ የሰው ጥላ ይ"መለከትና “ምንድነው ይኼ? በዚህ ቦታ ሌላ ሰው አለ እንዴ?” ብሎ ሲጠይቅ “ቀድሞ ዘማዊ በነበርሁበት ጊዜ የወለድኋት ልጄ ናት። እናቷ አኹን ከእግዚአብሔር ጋር ስለኾንህ አሳድጋት ብላኝ ነው። እኔን ከቀበርህ በኋላም እርሷን አግብተኽ ነው የምትኖረው” በማለት ይመልስለታል። ልብ አድርጉ ከበአቱ ካስወጣው በኋላ እንዴት እያለሳለሰ እየጣለው እንደኾነ። ሙሴም እንዴት ይኽ ይኾናል። እኔ መነኲሴ ነኝ። አላገባምእያለ ቢከራከረውም ተው እንጂ እንደሱ አትበል፣ ሙሴ አግብቷል፣ አብርሐምም አግብቷል፣ እዮብም አግብቷል ሀብታምም ነበር እያለ ከኹለት ቀናት በኋላ ግን አሳመነው። ከዚያም በኋላ ኾለቱን አጋባቸውና (ሙሴን እና ሌላኛውን ሰይጣን)፣ ሙሴም ያንን አባት (ሰይጣን) ሲሞት ቀበረው። የሰመመን እንቅልፍ መጥቶበትም ሲነቃ ያኹሉ ያየው ነገር ባዶ ነበር። ቤቱም ኾነ መቃብሩ ሚስቱም የሉም። ሙሴም ደነገጠ። እጅግ በጣም እያዘነ ከዚህ በኋላማ ምን አደርጋለሁ ወደከተማ ልኺድና ስንቄን ይዤ መጥቼ ተጋድሎዬን ልቀጥል ብሎ አስቦ ይኼዳል።
§  ሰይጣን ግን ብዙ እንዲያስብ ለሙሴ እድል መስጠት አልፈለገምና  ደግሞ እንደባለጸጋ ኾኖ በፈረስ ላይ ተቀምጦ ጠበቀውና ወደየት እንደሚኼድ ጠይቆት ከርሱጋር አብረው ወደከተማው መኼድ ጀመሩ። የከተማው ጫፍ ላይ እንደደረሱም፣ ያሰውዬ ሙሴን “በዚህ መንደር ያሉ ሰዎች ደጎች ናቸውና ከዚህ ከግንቡ ዳር ቆያቸው፣ የምትሻውን ይሰጡኻል። ሰላም ኹን” ብሎ ተሰናብቶት ኼደ። ከዚያም አካባቢ አንዲት ሴት ወጣችና ተመለከተችው። ምን እንደሚሻም ጠየቀችው። እርሱም  የሚሻው ስንቅ እንደኾነ ነገራት እርሷም ወደቤቷ አስገባችውና የሚሻውን እንዲበላ ሰጠችው። ከጠገበም በኋላ ሲጨዋወቱ ስለሕይወቱ ሲነግራት እርሷም መልሳ “አኹንኮ አግብተሃል፣ እኔን ደግሞ እንደምታየኝ ብጨኛ ነኝ፣ አግባኝ” አለችው። እርሱም እንደዚያ ከኾነማ ምን ገዶኝ ይልና ይስማማል። እየተጨዋወቱ ውድቅት ሲያልፍ በልጅቷ እየተሳበ መምጣቱን ተረዳችና “እንግዲህ እኔን ለማግባት የምትፈልግ ከኾነ አይኹድ መኾን አለብህ። ምክንያቱም እኔ ይሁዲ ነኝ። በዓለም ላይ ራሱ ያሉት ክርስቲያኖች ይሁዲ ትክክል መኾኑ አውቀው ይሁዲ እየኾኑ ነው።” ስትለው ሙሴ ተቀበላትና አምላኩን ካደ። ልብ አድርጉ ሰይጣን እንዴት በጥበብ አስወጥቶ እየተጫወተበት እንዳለ።
§  ከዚህ በኋላ ሲነጋ ተያይዘው ለሰው የሰጠኹት ገንዘብ አለ ብላው ነበርና ያንን ሊያመጡ ጉዞ ጀመሩ። ከብዙ ድካም በኋላ በረሐውን እያቋረጡ ሳለ ሙሴ ደከመው። ሴቲቱ ግን “እኔ ሴቷ እንኳ እንዲህ እየተጓዝሁ በል ተነስ ተጓዝ ” ብትለውም ደክሞትነበርና አልቻለም። ከዚያም በቅርብ ከተማ ካለ ልይ ብላው ወደተራራ ወጣች። ከተራራውም ላይ ኹና እየጨበጨበችበት “ሙሴ እንግዲህ ዋጋ የለህም። ምንኩስናህን ጠለህ አግብተሃል። አምላክህን ክደኸዋል። እንግዲህ ምህ ይበጅኻልማን ያድንሃል” እያለ አላገጠበትነ ተሰወረው። ሙሴ ግን በዚያ በኾነበት ነገር ኹሉ እጅጉን አዝኖ የሚገባበት ጠፋው። ምርር ብሎ እያለቀሰ እግዚአብሔር እንዲምረው እየተናዘዘ ከ15 ዓመታት በላይ በዚያ ቆየ። ከዚያም መልአከ እግዚአብሔር ተገልጦ “ሙሴ እግዚአብሔር ንስሐህን ተቀብሏል። ከሦስት ቀናት በኋላ ታርፋለህና ከባህታውያኑ ማኅበር አንድ ሰው ወዳንተ ነገ ይመጣል” አለው። እንደተባለውም በበነጋው አንድ ሰው ወደርሱ መጣና ወደ ማኅበረ ባሕታውያን ወሰደው። ሙሴም በዚያ ዐጽመ ቅድሳንን ለመሳለም እንደገባ በዚያው በሰላም ዐረፈ። ልብ አድርጉ እግዚአብሔር በቸርነቱ ባይረዳው ኖሮ ሙሴ በሰይጣን የማታለል መንገድተጉዞ አምላኩንም ክዶ ዋጋውን አጥቶ በቀረ ነበር። ስለዚህም ደቀ መዝሙር ጉዞውን በማስተዋል ማድረግ ይገባዋል። ይቀጥላል።

©ን መልኩ ይፍሩ 28/ 2010 .ም ጎር/ ኢጵያ

ረቡዕ 29 ኖቬምበር 2017

“ ደቀ መዝሙርነት ”(ክፍል ሁለት)



በስመ ወወልድ ንፈስ ቅዱስ አዱ አላክ ን።

(በዲ መል ይፍሩ ውሉደ ርሃ)

በቀደመው ክፍል ላይ ደቀ መዝሙር ማለት ማለት እንደኾነ እና ደቀመዝሙርን እውነተኛ ደቀ መዝሙር የሚያደኙትን ነገሮች መመልከት ጀምረን ነበር። ደቀ መዝሙር እውነተኛ የኾነ ዋጋን ለማግኘት እና እውነተኛ ደቀመዝሙር ከኾነ የተወዳጁን መምህሩን ቤት ጠብቆ የሚያስጠብቅ፣ አክብሮም የሚያስከብር እንደኾነ፤ እኛም የኹላችን መምህር መድኅን ዓለም ክርስቶስ የከፈለልንን ዋጋ ተመልክተን ሕንጻ መንፈስ ቅዱስ የኾነውን ሰውነታችንን በንስሐ እያነጻን በስጋወደሙ ማደስ እንደሚገባን፣ ክርስቶስ ውድ ዋጋ የከፈለባትን ሰማእታት መራራ ሞትን የታገሱላትን ቤተክርስቲያን እጅግ በጥንቃቄ እንድንጠብቃት ያስፈልጋል።
እውነተኛ ደቀ መዝሙር፦
v  የመምህሩን እና የቀድሞ ርቱዓን ደቀመዛሙርትን አሠረ ፍኖት መከተል እና እነርሱን መምሰል አለበት።
o   በዚህች ምድራዊት ገነት እንደኾነች ሀገራችን ውስጥ በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ለብዙ ዘመናት ሲሰጥ የቆየው የአብነት ትምህርት ወደዚህ ትውልድ የደረሰው በቅዱሳኑ ጸሎት እና በደቀመዛሙርቱ ትጋት፣ የቀደሙ መምህራኖቻቸውን አሠረ ፍኖት በመከተላቸው ነው። ደቀ መዝሙር የመምህሩን እና የቀደሙትን ርቱዓን ደቀመዛሙርት አሠረ ፍኖት በትክክል የሚከተል እና እነርሱን የሚመስላቸው ከኾነ የመምህሩን ትምህርት በነበረበት አጽንቶ ማስቀጠል ይችላል።
o   ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ኤልሳዕን ስንመለከተው፣ የመምህሩን አሠረ ፍኖት በሚገባ ሲከተል እና መምህሩን ሲመስለው እናገኛለን። እንደውም በሚገርም ኹኔታ መምህሩ ከርሱ በሚለይበት ወቅት የለመነው ነገር የመምህሩ ጸጋ በርሱ ላይ እጥፍ ኹኖለት እንዲያድርበት እና  የርሱን መንገድ እንዲያስቀጥል ነበር። ከ ዚህም የተነሳ መምህሩ ቅዱስ ኤልያስ “ትልቅ ነገር ለምነሃል። ነገር ግን ከአንተ በምወሰድበት ጊዜ ብትመለከት ይኾንልሃል” ነበር ያለው።
o   ቅዱስ ኤልሳዕም ይኽን አምኖ እንደተባለው አደረገና የቅዱስ ኤልያስን በጎናጸፊያ ተቀብሎ ኤልያስ ከፍሎት ያለፈውን ባህረ ዮርዳኖስ በስሙ ከፈለው። ኤልያስ አንስ ሙት ሲያስነሳ ኤልሳዕ ግን ኹለት ሙት ነበር ያስነሳው። የመጀመሪያውን መሕይወተ ሥጋ ሳለ ሲኾን ሌላኛውን ግን የሞተውን ሰው ሊቀብሩት ከጉድጓድ ሲያስገቡት በዚያ ጉድጓድ የነበረው የኤልሳዕ አጽም በነካው ጊዜ ወዲያውኑ ተነስቷል።ነቢየ እግዚአብሔር ለእግዚአብሄር ይቀና እንደነበር ኹሉ ቅዱስ ኤልሳዕም ፍጹም ቀናተኛ ነበረ። ቅዱስ ኤልያስ ለእውነት ሲል እንደተሰደደ ኹሉ ቅዱስ ኤልሳዕም ፍጹም እውነትን ለማጽናት የተጋ ቅዱስ ነበር።
o   እውነተኛው መምህር ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋእለ ሥጋዌው ሲመላለስ ኃጢአተኞችን ሳይጸየፋቸው ከነርሱ ጋር እያሳለፈ  ወደ ሕይወት ይጠራቸውና ያድናቸው፣ ለመንግስቱም ምስክር ያደጋቸው ነበር። በዚህም የተነሳ እነዚያ በሰዉ ኹሉ ሰንድ ይጠሉ የነበሩ ልባቸው በክርስቶ ስ ፍቅር እየነደደ ሳይሳሱ ሥጋቸውን ለሞት፣ ለእሳት፣ የአውሬ ይሰጡ ነበር። በዚህም ክርስቶ ስን መስለውታል። ደቀ መዝሙር መምህሩን ከመሰለ፣ መምህሩን የሚያስደስቱን ነገሮች ለማድረግ የግድ የመምህሩን ትእዛዝና የመምህሩን ከአጠገቡ መኖር አይጠብቅም። በኼደበት እና በኖረበት ቦታ ኹሉ እንደመምህሩ የቀና አነዋወርን ለመኖ ር የተጋ ይኾናል። መጽሐፍ በጊዜውም ያለጊዜውም ጽና የለው ለዚሁ ነው።
o   መምህራችን ኢየሱስ ክርስቶስን መምህራችን ነህ ካልነው እና እኛም ለክርስቶስ ደቀመዛሙርቱ እንባል ዘንድ እርሱን መምሰል ይጠበቅብናል። እርሱ የወደዳቸውን ኹሉ መውደድ፤ እንርሱ የሚደሰትበትን በጊዜውም ኾነ አለጊዜው ለማድረግ መትጋት ይጠበቅብናል። ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ ሲነግረን
“እኔ ክርስቶስን እንደምመስል እኔን ምሰሉ።” /1ኛ ቆሮ11፥1 / በማለት ነግሮናል። ክርስቶስን መምሰል ማለት በግብር ነው። እርሱ ያደረገውን ማድረግ። ጌታችን ቀን በትጋት ሲያስተምር ከዋለ በኋላ ምሽቱን በጸሎት ያሳልፋ። እውን ይኽን የሚያደርገው ከዚያ ጸሎት የሚጠቀመው ነገር ኑሮ ይኾን? አይደለም። ዳሩ ግን እኛ እርሱን አብነት አድርገን እንደርሱ በጸሎት የጸና የተጋ ሕይወት እንዲኖረ ን ለማስተማር እንጂ እርሱማ ስጡኝ አይል ሰጭ፣እከብር አይል ክቡር፣ የማይነጥፍበት ባዕል ነው። ፈጣሬ ዓለማትን ያደረገውን ተመ ልክተን በሕይወት በመተርጎም ደቀ መዝሙርነታችንን በሥራ በመግለጥ ምስክርነታችንን እውነት ለማድረግ ከአኹኑ መጀመር ይገባናል። ለዚህም የቅዱሳኑ ኹሉ ጸሎት እና  የወላዲተ አምላክ አማላጅነት ይርዳን። አሜን።
v  መምህሩ ለሚሰጠው እና ለቆመበት ዓላማ ሳያወላውል ጸንቶ መቆም ይገባዋል
o   ደቀ መዝሙር አስቀድመን እንደተናገርነው መምህሩን መስሎ ነው የሚኖረው። ስለዚህም በመምህሩ መንገድ እስከተጓዘ ድረስ መምህሩን ያገኙት ነገሮች ኹሉ፣ ከዚያም በላይ የኾኑ ነገሮች ስለሚገጥሙት ለዚያ ባለመሸነፉ በዓላማ ጽናት መቆም ይገባዋል። በዓላማ ጽናት መቆም ተብሎ ሲነገር እንደቀላል የምናስበው ነገር እንዳልኾነ ልብ ልንል ያስፈልጋል።
o   መድኅን ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ስለዚህ ነገር ሲነግረን ቅዱሳን ሐዋርያትን “እንደበጎች በተኲላ መኻከል እልካችኋለሁ” ብሎ ተናግሯል። ይኽን የነገራቸው በሚጓዙበት ጎዳና ላይ የሚገጥማቸውን ነገር ኹሉ ተመልክተው ከዓላማቸው ጽናት እንዳይታጎሉ ለማስተማር ነው። ደቀ መዝሙር ኹልጊዜም የሚገጥመውን ፈተና እንደትምህርት ቤት በመቊጠር ወደዓላማው በፍጥነት የሙጓዝ ነው።
§  ይኽን በደንብ እንድናስብበት የሚያደርገንን ምሴተ ሐሙስን ማስታወስ ያስፈልጋል። በምሴተ ሐሙስ ጌታችን ተግቶ እየጸለየ ተጨንቆ ሳለ ደቀመዛሙርቱ ግን ተኝተው ነበር። እርሱም ቀሰቀሳቸውና “ወደፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ፣ የሰው ልጅ ተላልፎ ይሰጥ ዘንድ ሰዓቱ ደርሷል” ካላቸው በኋላ ወዲያውኑ ይሁዳ ከወታደሮችና ከፈሪሳውያን ጋር መጣ። ካንተ አልለይም እያለ በእመነት ይናገር የነበረው ጴጥሮስን ጨምሮ ኹሉም ቢኾኑ ከፍቊረ እግዚኧእ ቅዱስ ዮሐንስ በቀር ጸንቶ ለሽልማት የበቃ  አልተገኘም። ፍቊረ እግዚእም መከራ መስቀሉን በመመልከቱ የተነሳ እድሜ ዘመኑን በሐዘን ተዘብሮ ስለኖረ ቊጾረ ገጽ በመባልም ተጠርቷል። እንደቅዱስ ዮሐንስ ፍቊረ እግዚእ ውድ የኾነችውን ስጦታ ለመሸለም እስከ ዓላማ ድረስ መታገስ እና መጽናት ያስፈልጋል። ለዚህም የቅዱሳኑ ኹሉ እና የድንግል ማርያም ጸሎት አይለየን።በቀጣዩ ክፍል የቀሩትን ነገሮች እንመለከታለን። ይቆየን።ይቀጥላል። 
                                                ©ን መልኩ ይፍሩ 
                                                    21/ 2010 .
                                                        ጎር/ ኢጵያ

ማክሰኞ 28 ኖቬምበር 2017

“ ደቀ መዝሙርነት ”(ክፍል አንድ)




በስመ ወወልድ ንፈስ ቅዱስ አዱ አላክ ን።
(በዲ መል ይፍሩ ውሉደ ርሃ)
የተወደዳችሁ የእግዚአብሔር ልጆች የእግዚአብሔር ሰላም በያላችሁበት ይብዛላችhu። ለዛሬ ስለደቀመዝሙርነት በጥቂቱ እንነጋገራለን።

ደቀ መዝሙርነትን የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት “የሃይማኖት ተማሪ፣ ተከታይ” በማለት ይገልጸዋል። እንደአጠቃላይ ለኛ ትምህርት እንዲያመቸን ግን ደቀ መዝሙር የሚለውን እንደሚከተለው እንፈታዋለን።
ደቀ መዝሙር ማለት መምህሩ በኼደበት የሚኼድ፣ በዋለበት ውሎ  ባደረበት የሚያድር፣ በመምህሩ ምክርና ትእዛዝ የሚመራ፣ መምህሩን ለመታዘዝና ለማገልገል የተጋ እና የነቃ ነው። ደቀመዝሙር ሁልጊዜም ቢኾን ለማገልገል የተጋ እና የነቃ ትሑት የኾነ፣ ለመምህሩም ያለውን ፍቅር በሥራ (በመታዘዝ እና ይኽን በመሰለው ኹሉ) የሚገልጽ ነው። ስለደቀመዝሙርነት እና ስለደቀ መዝሙር ምንነት በመጽሐፍ ቅዱስ በተለያዩ ክፍሎች በቅዱሳኑ ሕይወት ተቀምጦ እናገኘዋለን።
ለምሳሌም ያህል ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስ ኤልሳዕን ደቀመዝሙሩ አድርጎ እንደጠራው እንመለከታለን።
“ ከዚያም ሄደ፥ የሣፋጥንም ልጅ ኤልሳዕን በአሥራ ሁለት ጥማድ በሬዎች ሲያርስ፥ እርሱም ከአሥራ ሁለተኛው ጋር ሆኖ አገኘው። ኤልያስም ወደ እርሱ አልፎ መጐናጸፊያውን ጣለበት። በሬዎቹንም ተወ፥ ከኤልያስም በኋላ ሮጦ። አባቴንና እናቴን እስማቸው ዘንድ፥ እባክህ፥ ተወኝ፥ ከዚያም በኋላ እከተልሃለሁ አለው። እርሱም፦ ሂድና ተመለስ ምን አድርጌልሃለሁ? አለው። ከእርሱም ዘንድ ተመልሶ ሁለቱን በሬዎች ወስዶ አረዳቸው፥ ሥጋቸውንም በበሬዎቹ ዕቃ ቀቀለው፥ ለሕዝቡም ሰጣቸው፥ በሉም እርሱም ተነሥቶ ኤልያስን ተከትሎ ሄደ፥ ያገለግለውም ነበር። ”/1ኛ ነገ 19፡19-21/

ለነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ኤልሳዕም ግያዝ የሚጋል ደቀ መዝሙር እንደነበረው ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል። ግያዝም ኤልሳዕ በላከው ቦታ ኹሉ እየተላከ፣ ያዘዘውንም እያደረገ ያገለግለው እንደነበር እንመለከታለን። ሐዲስ ክዳንም ላይ ስንመጣ ቅዱሳን ሐዋርያት ጌታችን በዋለበት እየዋሉ፣ካደረበት እያደሩ፣ እየታዘዙት ቃሉንም እየሰሙ አብረውት ከርሱ ሳይለዩ  እንደቆዩ ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል። እነርሱም ጌታችን ካረገ በኋላ እንኳን በነበራቸው ሕይወት የመምህራቸው ደቀመዛሙርት መኾናቸውን አሕዛብ እንኳን እስኪመሰክሩላቸው ድረስ የተገለጠ ምግባር ነበራቸው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ቅዱስ ጢሞቴዎስን ጨምሮ ደቀመዛሙርት ነበሩት።
ታዲያ እንዲህ የምንናገርለት ደቀመዝሙርነት እንደምን ያለ ሰብእናን የተላበሰ ይኾን? ምን ዓይነት ነገር ያለበት ይኾን? እውነተኛ ደቀመዝሙርስ መለያው ምንድነው? ይኽን እና ሌኦችንም የሚነሱብንን ጥያቄዎች በሚከተለው መልስ እናገኝባቸዋለን።
እውነተኛ ደቀመዝሙር ኹልጊዜም፦
v  የጌታውን(የመምህሩን) ቤት እና ተማሪዎችአክብሮ የሚያስከብር፣ ጠብቆ የሚያስጠብቅ  ነው።
o   ደቀ መዝሙር ኹጊዜም ቢኾን የሚኖርባትን የመምህሩን ቤት በቃልም በግብርም ማስጠበቅ ይገባዋል። ያቺን ቤት መምህሩ እዚያ ያለችበት ቦታ ላይ ለማድረስ እና ለማቅናት እጅግ ብዙ ዋጋ የከፈለባት ናት። በተለይም በሀገራችን ያለውን የቆሎ ትምህርት የአብነት ትምህርት ስንመለከት፣ መምህራኑ ከእድሜያቸው ጀምሮ ያንን ጉባኤ ቤት ለማቆም እና  ተማሪዎችን ለማስተማር እጅግ ብዙ ዋጋ ይከፍላሉ። ከአላውያን የሚደርስባቸውም እንግልት እና ግፍ የሚነገር አይደለም። በዘመነ ሰማእታት አዲስ የሚከረሰተኑ(ክርስቲያን የሚኾኑ) ምእመናንን በግልጽ ሲያስተምር የሚገኝ የቤተክርስቲያን መምህር ይገደል ስለነበር እና የሚማሩትንም ክርስቲያኖች ስለክርስትና  ሳያውቁ እንዳይቀሩ ሲባል በዋሻ፣በካታኮምፕ ውስጥ ያስተምሯቸው ነበር።
o   የክርስቶስ ደቀመዛሙርት ለመኾን የምንሻ ከኾን፣ የርሱን የመምህራችንን ቤት ዳግመኛም የቅዱሳን ሊቃውን ት ቤት የኾነችውን ቅድስት ቤተክርስቲያንን  ልንጠብቃት ያሻል። እርሷን ለመመስረት ሲል የቤተ ክርስቲያን ራስ ኢየሱስ ክርስቶስ የከፈለውን የመከራ መስቀል ዋጋ እያሰብን አክብረን እንደቅዱሳኑ ልናስከብራት ያስፈልጋል። ቅዱሳን መራራ ሞትን እንኳን እንዲታገሱ ያደረጋቸው የመምህራቸውን ቤት ቤተክርስቲያንን አንድም ሕንጻ ሥላሴ የኾነውን ሰውነታቸውን ላለማስደፈር፣ አክብረው በማስከበር ነው።
“በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ።” /ሐዋ 20፡28/
o   ክርስቶስ ቤተክርስቲያንን ስለወደዳት ለራሱ እንኳን ሳይሳሳ ደሙን ከፍሎ እንደወደዳት በሥራ ገለጸ። እኛ ደግሞ እንዲህ የተጠነቀቀላትን ቤት እንዴት ልንጠነቀቅላት እንዲገባ  ልብ ይሏል።
o   ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ ነገረ ሥጋዌን ባስተማረበት ትምህርቱ ላይ ሲናገር፣ የክርስቶስ በሥጋ መገለጥ ልዩ ስለኾነ ቸርነቱን በማሰብ ልንደነቅ ያስችል ይኾናል እንጂ እንዴት ይኾናል ብሎ ሊያስክድ እንደማይችል አሕዛብን እና አይሁድን እየገሠጸ ያስረዳል። የተገለጠው አዳኙ አኹን በተለየ መንገድ ሥጋን ተዋሕዶ ተገለጠ እንጂ ቀድሞውንም ከመገለጡ በፊት በትልቆቹም በትንሾቹም ፍጡራን በውስጥ በአፍአ ይኖር የነበረ  ነው። ስለዚህ ይኽ ድንቅ አምላክ የኛንም ሰውነት ማደሪያው አድርጎ በውድ ዋጋ በንጹሕ ደም ገዝቶታልና ይህን የቅዱሱን  ቤት አክብረን ማስከበር፣ ጠብቀን ማስጠበቅ ይገባናል።
o   ይኽን ቤተመቅደስም ለማስጠበቅ የምንጠቀምባቸውን መንገዶች ቅዱስ መጽሐፍ እንደነገረን እንዲህ መዘርዘር እንችላለን።
§  ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብ የቅዱሳንን ሕይወት በመመልከት ራስን በዚያ ማነጽ ይገባል
§  ኃጢአትን በመናዘዝ ራስን ከሸክም ነጻ በማድረግ ለቅዱሱ ማደሪያ የኾነውን ቤተመቅደስ በጎ መዓዛን እንዲኖረው፣ እንደእጸ ሕይወት የማይሰለች የሚናፈቅ፣ መልካም መዓዛ እንዲኖረው ለማድረግ እየጣርን ቅዱሳኑን እና ራሱን ቅዱሱን እንድረዱን መጠየቅ ይገባናል።
§  ከቅዱስ ምሥጢር ኹልጊዜም ልንለይ አይገባም። ቅዱስ ምስጢርን መሳተፍ ጌታችን በቅዱስ ወንጌል እንደነገረን፣ ቅዱሱ በቤቱ ገብቶ ከእኛ ጋር እራት እንዲበላ እና ሰላምን እንዲሰጠን ሕይወትን እንዲሰጠን ያደርጋልና ይኽን ልናስብበት እና ልንተጋበት ይገባል።
ይቆየን !
በቀጣዮቹ ክፍሎች ሌሎቹን ነገሮች እናነሳቸዋለን።አምላከ ቅዱሳን ጾሙን የበረከት እና የንስሐ፣ ወደርሱም የምንቀርብበት ያድርግልን። 
ን መልኩ ይፍሩ©
 19/ 2010 .
 ጎር/ ኢጵያ