በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።
ጾም ፦ ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ የምናስገዛበት ምግባር ነው። ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ ሥጋ በመንፈስ ላይ ሊሰለጥን እንደሚታገሉ ገልጦልናል። እንዲሁም ”ቅንኡ ለእንተ ተአቢ ጸጋ-ለምትበልጠው ጸጋ ቅኑ/ትጉ/” በማለት ስለነገረን የሥጋን ፈቃድ በነፍስ ፈቃድ ድል አድርገን ለነፍስ ለማስገዛት ልንተጋ ያስፈልጋል።
ጾም እና መባልእት /ምግቦች/
በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሥርዓት መሠረት በጾም ወራት የምንመገባቸው እና
የማንመገባቸው ምግቦች አሉ። ለዚህም መሠረት የሚሆነን ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ፦
“ጉልበቶቼ በጾም ደከሙ ሥጋዬም ቅቤ በማጣት ከሳ” /መዝ108(109) ፡24/
በማለት የሚነግረን ነው። ሌሎችም ይህን የመሰሉ መሠረት የሚሆኑን የቅዱስ መጽሐፍ ቃላት አሉ።
ሀ/በጾም ወቅት የማይበሉ መባልእት፦
በወርኃ ጾም የማይበሉት መባልእት ጥሉላት ነክ የሆኑ ምግቦች ናቸው። የእሊህም ምግቦች መከልከል ምክንያት ሰውነታችንን የሚገነቡ እና ለሰውነት መታደስ ትልቅ አስተዋጽኦ ያላቸው መባልእት ስለሆኑ ነው። በዚህም ውስጥ ሥጋ፣ ቅቤ፣ ወተው፣ ወዘተ የመሰሉትን ይካተቱበታል።በሥጋ ሥር የዓሳን ጉዳይ እንደሚከተለው እንመልከት።
ዓሣ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሊቃውንት ዘንድ ለብዙ ጊዜያት ሲያከራክር የቆየ ጉዳይ ነው። ይህም ሠለስቱ ምእት በፍትሐ ነገሥት ፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 15 ላይ “ኢትብልኡሥጋ ዘእንበለ ዓሣ”ያሉትን በመያዝ ነበር የሚከራከሩት።
አንዱ ወገን “ዘእንበለ ዓሣ”የሚለውን ከዓሣ በቀር ሌላ ሥጋ አትብሉ የሚል ሲሆን
ሌላኛው ደግሞ “ዘእንበለ ዓሣ”የሚለውን ዓሣንም ጨምሮ ሥጋ አትብሉ የሚል ነው።
የ“ዘእንበለ ዓሣ”ትርጉም ሁለት አይነት ስለሆነ እንዲህ ክርክር ሊያስነሳ የሚችል ቢሆንም እንኳን ለምሳሌ ያህል በወርኃ ጾም ዓሣን እንዳንበላ የሚያደርጉን ሁለት መሠረታዊ ምክያቶችን እንመልከት።
ምክንያት 1/ በዚህ አንቀጽ “ዘእንበለ ዓሣ” ተብሎ የተነገረው ክርክር ቢያስለሳም እንኳን ሠለስቱ ምእት በሌላ አንቀጽ “ለእመ ተገዓዝክሙ በጾም አድልዉ ለጾም-በጾም ምክንያት በተከራከራችሁ ጊዜ ለጾም አድሉ” በማለት ተናግረዋል።
ስለዚህም ለዚህ ክርክር መቋጫው የምናደርገው ለጾም ማድላትን ነው። ስንኳን በጾም ወራት፣ በመደበኛው ቀንም ቢሆን ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ “ሥጋ መብላቴ ወንድሜን የሚያሰናክለው ከሆነ ሥጋ ባልበላ ይሻለኛል” ብሏል።
ምክንያት 2/ ዓሣ በውስጡ የያዛቸው ንጥረ ምግቦች/nutrients/ በሳይንሱ ዓለም የተደረጉ ጥናቶች እንዳረጋገጡትእጅግ ገንቢና ጠጋኝ የሚባሉ ናቸው። የጾመ መሠረታዊው ዓላማ ደግሞ ቅዱስ ዳዊትም እንደተናገረው ሥጋን ማድከም እና ነፍስን በሥጋ ላይ በምግባር ማሠልጠን ማበርታት ስለሆነ የዓሣ ሥጋን መመገብ ደግሞ ከዚህ የጾም ጋር ፈጽሞ አትስማማም።
በጾም ወቅት ዓሣን መመገብ ማለት ሥጋን ለነፍስ ፈቃድ አስገዛለሁ ብለው እየደከሙ ዳሩግን ይህን ድካም መልሶ ከንቱ ማድረግ ነው። ስንኳን የዓሣ ሥጋ ይቅርና ከአትክልት ምግቦችም፣ ከጥራጥሬም ቢሆን ሰውነትን የሚያበረታታ እና እጅግ ገንቢ ጠጋኝ የሆኑ ምግቦችን በተለይም በጾም ወቅት ከመመገብ ልንከለከል ያስፈልጋል። እንዲህ ካላደረግን ሥጋችንን ለነፍሳችን እናስገዛለን ብለን የምንሠግደው ሥግደት፣ የምንጸልየው ጸሎት የምናለቅሰው ልቅሶ ከንቱ ድካም ይሆንብናል።
እግዚአብሔር የሚወደውን አይነት ጾም ጹመን የጾሙን በረከት ያድለን ዘንድ የቅዱሳኑ ሁሉ ጸሎት ይርዳን።
ምንጭ፦ መርሐ ጽድቅ ባህለ ሃይማኖት
፦ፍትሐ ነገሥት
ወስብሐት ለእግዚዕብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር አሜን።
ይቆየን።
©ዘዲያቆን መላኩ ይፍሩ
ሰኔ 29/2009 ዓም
አዲስ አበባ/ ኢትዮጵያ